2010–2019 (እ.አ.አ)
ከእንግዲህ ወዲያ... እንግዶች አይደላችሁም
ኦክተውበር 2013


ከእንግዲህ ወዲያ... እንግዶች አይደላችሁም

በዚህች ቤተክርስቲያን ውስጥ፣ እንግዳዎች እና የሚወገዱ የሉም። ወንድሞችና እህቶች ብቻ ናቸው ያሉት።

አብዛኛዎቻችን በአንድ ጊዜም ይሁን በሌላ ለእኛ አዲስ የሆነ፣ ልዩና የማንተማመንበት ጉዳዮች ላይ እራሳችንን እናገኛለን። ከአምስት አመት በፊት ፕሬዘደንት ሞንሰን እኔ እንደ አጠቃላይ ባለስልጣን እንዳገለግል ጥሪ በሰጡኝ ጊዜ ይህም ሁኔታ በቤተሰባችን ላይ ደረሰብን። ባለቤቴ እና እኔ ልጆቻችን ስለዚህ ለውጥ በሚያውቁበት ጊዜ እንዴት እንደደነገጡ እናስታውሳለን። የ16 አመት ወንድ ልጃችን እንዲህ አለ፣ “ይህ ችግር አይደለም። እናተ ሂዱ፣ እኔ በዚህ እቀራለሁ!”

ከዚያም ከእኛ ጋር አብሮ ለመሄድ እና በህይወቱ የመጡ አጋጣሚዎችን በእምነት ለማቀፍ ተስማማ። ባለፉት ጥቂት አመታት ውስጥ በአዲስ ቦታዎች መኖር ለቤተሰባችን የሚያስደስት እና የሚያስተምር አጋጣሚ ነበር፣ ይህም የሆነውም በኋላኛው ቀን ቅዱሳን ተቀባይነትና መልካምነት ምክንያት ነው። በተለያዩ አገሮች ውስጥ ስንኖር፣ በምድር ውስጥ ያለው የእግዚአብሔር ህዝብ አንድነት እውነተኛ እንደሆነ ለማወቅ ችለናል።

ሀላፊነቴ በብዙ አገሮች እንድጓዝና በብዙ ስብሰባዎች በመሪነት እንድገኝ ልዩ እድል ሰጦኛል። የተሰበሰቡትን ስመለከት፣ ብዙ ሀገሮችን፣ ቋንቋዎችን፣ እና ባህሎችን የሚወክሉ ብዙ አባላትን እመለከታለሁ። የወንጌል ዘመናችን አንዱ አስደናዊ ጉዳይ ቢኖር በጊኦግራፊ ክልልሎች ወይም በሀገር ቡድኖች የተገደበ አይደለም። ይህም አለማዊና ሁለንታዊ ነው። ይህም “ልጆቹን ከአለም አራት ማዕዘን”1 በመሰብሰብ ለእግዚአብሔር ልጅ መመለስ መዘጋጃ ነው።

የቤተክርስቲያኗ አባላት ልዩነት እየጨመረ ቢሆንም፣ ቅዱስ ውርሳችን ከልዩነታችን በላይ የተሻለ ነው። እንደ ቤተክርስቲያኗ አባላት፣ ወደ እስራኤል ቤት ለመግባት ችለናል። ለአንድ አይነት መንፈሳዊ ውርስ እኩል ወራሾች ሆነን ወንድሞችና እህቶች ሆነናል። እግዚአብሔር አብርሀምን ቃል እንደገባለት፣ “እና በስምህ በኩልም እባርካቸዋለሁ፤ ይህን ወንጌል የተቀበሉት ሁሉ በአንተ ስም ይጠራሉ፣ እና እንደ አንተ ዘር ይቆጠራሉ፣ እና እንደ አባታቸው ተነስተው ይባርኩሀል።”2

የቤተክርስቲያኗ አባል ለሆኑ በሙሉ ቃል ኪዳን ተገብቷል፥ “እንግዲያስ ከእንግዲህ ወዲህ ከቅዱሳን ጋር ባላገሮችና የእግዚአብሔር ቤተ ሰዎች ናችሁ እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም።3

በላቲን እንግዳ የሚባለው ቃል “ውጪ” ወይም “ከውጪ የመጣ”, የሚል ትርጉም አለው። ይህም አንድ ሰውን በስረ ነገሩ፣ በባህሉ፣ በአስተያየቱ፣ ወይም በሀይማኖቱ ምክንያት “ከውጪ የመጣ” በማለት ይመድባል። በአለም ውስጥ ቢሆኑም ከአለም ባልሆኑት የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት፣ አንዳንዴ ከውጪ እንደመጣን አይነትይሰማናል።እኛ፣ ከሌሎች ይበልጥ፣ ልዩ ናቸው ተብሎ ለሚታሰብባቸው በሮች እንደሚዘጉባቸው በእርግጥም እናውቃለን።

በዘመናት የእግዚአብሔር ህዝብ እንግዳ ለሆኑት ሰዎች ሁሉ ወይም እንደ ልዩ የሚመለከቷቸውን ሁሉ እንዲንከባከቡ ትእዛዝ ተሰጥቷቸዋል። በጥንት ጊዜዎች፣ እንግዳ እንደ መበለት እና ሙት ልጅ አይነት የእንግዳ ተቀባይነት ጥቅምን ያገኙ ነበር። እነደእነርሱም ፣ እንግዳ ለታላቅ አደጋ የተጋለጠ ነው፣ እናም ለመዳን የሚችለውም በአካባቡ በሚገኙ ሰዎች ጥበቃ ምክንያት ብቻ ነው። የእስራኤል ህዝብ ስለዚህ ርዕስ ቀጥተኛ መመሪያ ተሰጥቷቸዋል፥ “እናንተ በግብፅ ምድር እንግዶች ነበራችሁና ከእናንተ ጋር የሚቀመጥ እንግዳ እንደ አገር ልጅ ይሁንላችሁ፥ እርሱንም እንደ ራስህ ውደድ።”4

በምድር አገልግሎቱ፣ ኢየሱስም አስፈላጊ ከሆነው የእንግዳ ተቀባይነት በላይ የሚደረገውን ምሳሌ ያሳየ ነበር። ከህብረተሰብ የተወገዱት፣ እራሳቸውን ጻድቅ ነን ብለው በሚመለከቱት ንጹህ እንዳልሆኑ የሚታሰብባቸው ከእርሱ ርህራሄና ክብር አግኝተዋል። የትምህርቱንና የአገልግሎቱን እኩል ድርሻም ተቀብለዋል።

ለምሳሌ፣ አዳኝ ይኖርበት ከነበረው ባህል ተቃራኖ በመሆን የሰማርያ ሴትን በማነጋገር ውሀ እንድትሰጠው ጠየቃት። ከቀራጮች ጋር ለመመገብ ተቀመጠ። ለምጻምን ለመንካትና ለመፈወስም አልተጠራጠረም። የሮሜ አንድ መቶ አለቃን እምነት ተደንቆበትም፣ ለህዝቡ እንዲህ አለ፣ “በእስራኤል እንኳ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም።”5

ኢየሱስ ሀለንተናዊና ያለምንም ቅድመ ሁኔታ የሌለው ስጦታ የሆነውን ፍጹም ፍቅር ህግ እንድንከተል ጠይቆናል፥

“የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን?

“ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን?

“እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ።”6

በዚህች ቤተክርስቲያን ውስጥ፣ እንግዳዎች እና የሚወገዱ የሉም። ወንድሞችና እህቶች ብቻ ናቸው ያሉት። ዘለአለማዊ አባት እንዳለን ማወቅ በአለም ውስጥ ባሉት ወንዶች እና ሴቶች ሁሉ መካከል መገኘት ለሚገባው ወንድማዊነት እና እህታዊነት ተጨማሪ ስሜት እንዲኖረን ያደርጋል።

Les misérables በሚባለው የልብወልድ መፅሐፍ ውስጥ የሚገኝ ፅሁፍ እንደ እንግዳ የሚመለከቷቸውን ሰዎች የክህነት ባለስልጣኖች እንዴት መመልከት እንደሚገባቸው ያሳያል። ዦን ባልዦን ከእስር ተለቅቆ ነበር። ከብዙ ጉዞ ምክንያት ተደክሞ እና በራብንና ጥማት እየተሰቃየ፣ ምግብና ለምሽት የሚጠለልበት ቦታ ለማግኘት ወደ አንድ ትንሽ ከተማ ገባ። የእርሱ መምጣት ዜና ሲመጣ፣ በዚያ የሚኖሩት በሙሉ አንድ በአንድ በሮቻቸውን ዘጉበት። ምንም ሆቴል ወይም እስር ቤትም እርሱን ለመጋበዝ እምቢ አሉ። ተወገደም፣ ተባረረ፣ ተጋዘ። በመጨረሻም፣ በከተማው ኤጲስ ቆጶስ በር ላይም ወደቀ።

ኤጲስ ቆጶስም የቫልዣንን ታሪክ ያውቁ ነበረ፣ ነገር ግን ለማኙን ከእነዚህ የርህራሄ ቃላት ጋር ወደ ቤታቸው አስገቡት፥

“‘ይህ ቤቴ አይደለም፤ የኢየሱስ ክርስቶስቤት ነው። በሩ የሚገባበትን ስም እንዳለው የሜጥይቅ ሳይሆን ችግር እንዳለው የሚጠይቅ ነው። ተሰቃይተሀል፣ ርቦሀል እናም ጥምቶሀል፣ በመልካም ግባ።...ስምህን ለማወቅ ለምን ያስፈልገኛል? በተጨማሪም፣ አንተ ስምህን ለእኔ ከመንገርህ በፊት አውቄው ነበር።’

“[ቫልዦን] አይኑን በድንቀት ከፈተ።

“‘እርግጠኛ ኖት? ስሜን ያውቁ ነበር?’

“ኤጲስ ቆጶሱም ‘አዎን፣ ስምህ ወንድሜ ነው’ ብለው መለሱ።”7

በዚህች ቤተክርስቲያን ውስጥ፣ ዎርዶቻችን እና ቡድኖቻችን የእኛ አይደሉም። የኢየሱስ ክርስቶስ ናቸው። ወደ መሰብሰቢያ ቤቶቻችን የሚገቡት ማንኛዎችም ተቀባይነት ይሰማቸው። ሁሉንም ተቀባይነይ እንዲሰማቸው ማድረጉ በጣማስፈላጊ ነው።፡የምንኖርበት አለም ታላቅ ለውጥ ላይ ነው ያለው።፡ለመጓዝ የሚቻልበት፣ የግንኙነት መንገድ፣ እና የኢኮኖሚ አለማዊነት በቀላል የሚገኝ ስለሆነ፣ ምርድ ህዝቦች እና ሀግሮች የሚገናኙበት፣ እናም ከዚህ በፊት ተደርጎ በማይታወቅ ሁኔታ የሚቀላቀሉበት እንደ አንድ ትልቅ መንደር ሆናለች።

የአለማቀፍ ለውጡ የሁሉን ቻይ እግዚአብሔርን አላማ ያገለግላል። የተመረጡትን ከምድር አራት ማዕዘን መሰብሰብ የሚከናወነው ሚስዮኖችን ወደ ሩቅ አገሮች በመላክ ብቻ ሳይሆን ከሌሎች ቦታዎች ወደ ከተማዎቻችን እና ጎረቤቶቻችን በሚመጡበት ነው። ብዙዎች፣ ሳያውቁት፣ ወንጌሉን ወደሚሰሙበት እና ወደ እቅፉ ወደሚመጡበት በጌታ እየተመሩ ናቸው።

በዎርዳችሁ ወደ ወንጌል የተቀየረው የሚቀጥለው ሰው ከቅርብ ጓደኛችሁ መካከል የመጣ እንዳልሆነ የተረጋገጠ ነው። ይህንንም በእርሱ ወይም እርሷ አመለካከት፣ ቋንቋ፣ አለባበስ፣፣ ወይም በቁዳ ቀለም ለማወቅ ትችላላችሁ። ይህም ሰው በሌላ ሀይማኖት፣ በተለየ ባህል ወይም የህይወት አኗኗር ያደገ ይሆናል።

ጓደኝነት የክህነት ዋና አስፈላጊ ሀላፊነት ነው። የአሮናዊ እና የመልከ ጸዴቅ ክህነት ቡድኖች ከደጋፊ ድርጅቶች ጋር በኤጲስ ቆጶስ አመራ ስር እያንዳንዱ ሰው በፍቅር እና በደግነት ተቀባይነት እንዲያገኙ ያድርጉ። የቤት ለቤት እና የሴቶች የቤት ለቤት አስተማሪዎችም ማንም እንዳይረሳ ወይም ችላ እንዳይባል ያረጋግጣሉ።

በዎርዳችን እና በቅርንጫፎቻችን መንፈሳዊ አንድነትን ለመገንባት ሁላችን መስራት ያስፈልገናል።፡ክርስቶች አሜሪካን ከጎበኘ በኋላ በእግዚአብሔር ህዝቦች መካከል ፍጹም የሆነ አንድነት ምሳሌ ነበር። መዝገቡ እንደሚያስመለክተው “ላማናውያንም ሆኑ ማንኛውም ዓይነት በመደብ የተለዩ ሰዎች አልነበሩም፤ ነገር ግን ሁሉም በአንድነት የክርስቶስ ልጆች ነበሩ፣ እናም የእግዚአብሔርንም መንግስት ወራሾች ነበሩ።”8

አንድነት የሚገኘው ልዩ የሆኑ ወይም የደከሙ አባላትን ችላ በማለት ወይም በማስወገድ እና እንደ እኛ አይነት ከሆኑት ጋር ብቻ ግንኙነት በማድረግ አይደለም። ከዚህ በተቃራኒም፣ አንድነት የሚገኘው አዲስ የሆኑትን ወይም ልዩ እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን በማገልገል ነው። እነዚህ አባላት ለቤተክርስቲያኗ በረከቶች ናቸው እናም ጎረቤቶቻችንን ለማገልገል እና በዚህም ልባችንን ለማጽዳት እድል ያቀርቡልናል።

ስለዚህ፣ ወንድሞች፣ በቤተክርስቲያናችሁ በር ላይ የሚመጣውን ማንኛውንም የመቀበል ሀላፊነት የእናንተ ነው። በምስጋና እና ያለ መጥሌ ተቀበሏቸው። የማታውቋቸው ሰዎች ወደ መሰብሰቢያ ቤቶቻችሁ ከገቡ፣ በሙቅ ሰላምታ ተቀብሏቸው እና ከእናተ ጋር እንዲቀመጡ ጋብዟቸው። እነርሱ ወደ እናንተ እስከሚመጡ በመጠበቅ ሳይሆን እናንተ በመጀመሪያ ተቀባይነት ፍቅር እንዲሰማቸው በማድረግ እርዳታ ስጧቸው።

ከመጀመሪያው ሰላምታችሁ በኋላ፣ እነርሱን ለማገልገል የምትቀጥሉበትን መንገዶች አስቡባቸው። አንድ ጊዜ ለመስማት የማይችሉ ሴቶች ከተጠመቁ በኋላ፣ ሁለት አስደናቂ የሴቶች መረዳጃ ማህበር እህቶች ከተቀየሩት ጋር ለመነጋገር ለመቻል በጣት ለመነጋገር የሚችሉበት እንደተማሩ የሰማሁበት አንድ ዎርድ አለ። በወንጌል ወንድሞች እና እህቶች ለሆኑት ያለውን ፍቅር የሚያሳይ ምን አይነት አስደናዊ ምሳሌ ነው።

ማንም ለሰማይ አባታችን እንግዳ እንዳልሆነ እመሰክራለሁ። ለእርስይ ነፍሱ ውድ ያልሆነለት ማንም ሰው የለም። ከጴጥሮስም ጋር ይህን እመሰክራለሁ፣ “እግዚአብሔር ለሰው ፊት እንዳያደላ ነገር ግን በአሕዛብ ሁሉ እርሱን የሚፈራና ጽድቅን የሚያደርግ በእርሱ የተወደደ እንደ ሆነ በእውነት አስተዋልሁ።”9

ጌታ በመጨረሻው ቀን በጎቹን ሲሰበስብ፣ ለእያንዳንዳችን “እንግዳ ሆኜ ተቀብላችሁኛል” እንዲለን እጸልያለሁ።

ከዚያም ለእርሱም እንዲህ እንለዋለን፣ “እንግዳ ሆነህስ አይተን መቼ ተቀበልንህ?”

እና እርሱም እንዲህ ይመልሰናል፣ “ከሁሉ ከሚያንሱ ከእነዚህ ወንድሞቼ ለአንዱ እንኳ ስላደረጋችሁት ለእኔ አደረጋችሁት”10

በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።