2010–2019 (እ.አ.አ)
ታላቁ የወጣት ጎልማሶች ትውልድ
ኤፕረል 2015


ታላቁ የወጣት ጎልማሶች ትውልድ

አሁን የምንፈልገው በቤተክርስቲያኗ ታሪክ ውስጥ ታላቁን የወጣት ጎልማሶች ትውልድ። መላ ልባችሁንና ነፍሳችሁን እንፈልገዋለን።

በአለም ዙሪያ ስጓጓዝ ካገኘኋቸው ታላቅ ደስታዎች መካከል አንዱ ሚስዮኖችን ለማግኘትና ሰላም ለማለት ያገኘሁት እድል ነው። እነዚህ ታላቅ ሽማግሌዎችና እህቶች የጌታን ብርሃን ያንፀባርቃሉ እናም ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስና ባላቸው ፍቅርና ለእርሱ ባለቸው የተሰጠ አግልግሎት ሁሌም እነሳሳለሁ። ሁልጊዜ ከእነሱ ጋር እንጅ እጨባበጣለሁ እና አስደናቂ መንፈስና እምነታቸው ይሰማኛል፣ ለራሴ “እነዚህ አስገራሚ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችን እውነትም ተዓምር ናቸው!” እላለሁ።

በጥቅም 2002 (እ.አ.አ) አጠቃላይ የክህነት ስብሰባ ወቅት፣ ኤጲስ ቆጶሶችን፣ ወላጆችን እና ሚስዮን ሊሆኑ ያሉትን ለሙሉ ጊዜ የሚስዮን አገልግሎት “መስፈርቱን ከፍ እንዲያደርጉት” ጋበዝኳቸው።

ከዛ እንደዚህ አልኩኝ “የምንፈልገው…በቤተክርስቲያኗ ታሪክ ውስጥ የሚስዮኖች ታላቅ ትውልድ ነው። ብቁ፣ የሚያሟሉ፣ በመንፈሳዊነት የተዘጋጁ ሚስዮኖችን እንፈልጋለን። …

“…ሙሉ ልባችሁንና መንፈሳችሁን እንፈልጋለን። መንፈስ ቅዱስን የሚያዳምጡና ለሹክሹክታው መልስ መስጠት የሚያውቁ ጉልበት ያላቸው፣ የሚያስቡ፣ ፍቅር ያላቸው ሚስዮኖች እንፈልጋለን”1

ከ13 አመት በፊት ከነበረው ይልቅ አለም ዛሬ በብዙ መንገድ ፈታኝ ናት። ወጣት ወንዶቻችንና ሴቶቻችን ለሚስዮንና ለወደፊት የደስታ ሕይወት ዝግጅታቸው ላይ የሚያምታቱ ብዙ ነገሮች አላቸው። ቴክኖሎጂ ተንሰራፍቷል እናም ሁሉም በእጅ የሚያዝ የሰውን የእግዚአብሔር ቤተሰብ አትኩሮት ለመልካምም ሆነ ለታላቅ መጥፎነት የሚይዝ መሳሪያ አለው።

ዛሬ ማታ አሁን እያገለገሉ ላሉ፣ ወደ ፊት ለሚያገለግሉ፣ ጨርሰው ለተመለሱ ሚሲዮኖችና በቤተክርስቲያኗ ውስጥ ላሉት ለሁሉም ወጣት የወንድ ጎልማሶች እናገራለሁ። በዚህ አስደሳችና አስቸጋሪ የሕይወታችሁ አመታት ላይ ስትጓዙ የምለው ነገር እንዲገባችሁና በአስተውሎት እንድትመለከቱት እፀልያለሁ።

በቤተክርስቲያኗ ቀደምት አመታት ውስጥ፣ ሚስዮኖች ወደ ተልዕኮ ከመሄዳቸው በፊት በአጠቃላይ አመራር ነበር ቃለ መጠይቅ የሚደረግላቸው የነበረው። በአሁኑ ቀናት እንደ ሚስዮኖች ለማገልገል በኤጲስ ቆጶሳችሁና በካስማ ፕሬዘደንታችሁ ነው ቃለ መጠይቅ የሚደረግላችሁ እና ብዙዎቻችሁ በአጠቃላይ አመራር ቃል መጠይቅ ሳይደረግላችሁ ቀሪ ሕይወታችሁን ትኖራላችሁ። ይህም የሆነው ከ15 ሚሊዮን በላይ አባሎች ባሏት አለም አቀፍ በሆነች ቤተክርስቲያን ምክንያት ነው። ሁላችሁን በግል ለማወቅና እንደምንወዳችሁና እንደምንደግፋችሁ ለመናገር መቻል እንደምንመኝ ስነግራችሁ ለወንድሞቼም እንደምናገር አወቃለሁ።

ይሁን እንጂ፣ ጌታ ለእናንተ እንድንደርስ መንገዶች ሰጥቷል። ለምሳሌ፣ የአስራ ሁለት ሐዋርያት አንድ የሸንጎ አባል እያንዳንዱን ሚስዮን ወደ ተልዕኮ ይመድበዋል ወይም ይመድባታል። ምንም እንኳን ይሄ የሚደረገው እንደቀድሞው በአካል ባይሆንም፣ ቴክኖሎጂና ራዕይ በጋራ በመጣመር በሚያስደንቅ ሁኔታ የጠለቀና የግል ልምድ ይሰጣሉ። ይሄ እንዴት እንደሚሆን ልንገራችሁ።

የእናንተ ፎቶ በኮምፒተር ገፅ ላይ ኤጲስ ቆጶሳችሁና የካስማ ፕሬዘደንታችሁ ከሰጡት አንዳንድ ቁልፍ መረጃዎች ጋር ይመጣል። ፎቶዎቻችሁ ሲመጣ አይናችሁን እናያለን እና ለሚስዮን የብቁነት ጥያቄዎች የሰጣችሁትን መልስ እንከልሳለን። በዛ አጭር ጊዜ፣ በአካል ያላችሁና ለእኛ በቀጥታ የምትመልሱ ነው የሚመስለው።

ፎቶዎቻችሁን ስንመለከት፣ በሁሉም መንገድ ዛሬ አማኝ፣ ወጤታማ ሚስዮነ ለመሆን “ከፍ ያለውን መስፈርት” ማሟላታችሁን እናምናለን። ከዛ በጌታ መንፈስ ኃይልና በፕሬዘደንት ቶማስ  ኤስ ሞንሰን አመራር ስር ለቤተክርስቲያኗ 406 አለም አቀፍ የሚስዮን ቦታዎች ወደ አንዱ እንመድባችኋለን።

አይደለም፣ ከግላዊ የአንድ ለአንድ ቃለ መጠይቅ ጋር አንድ አይነት አይደለም። ነገር ግን ተቀራራቢ ነው።

ከቤተክርሰቲያኗ ዋና መምሪያ እርቀው ለሚገኙት የቤተክርስቲያን መሪዎች ለመድረስ የሚረዳን ሌላኛው መንገድ የቪዲዮ ጉባኤ ነው።

ያንን በማሰብ ሚስዮን ለማገልገል እየተዘጋጃችሁ ያላችሁትን፣ ጨርሳችሁ የተመለሳችሁትን እና ሁላችሁም ወጣት ጎልማሶችን አሁን ግላዊ የቪዲ ንግግር እያደረግን እንደሆነ በማሰብ ከእኔ ጋር ትንሽ ጊዜ እንድታሳልፉ እፈልጋለሁ። እባካችሁን ዛሬ ማታ ባላችሁበት ቦታ እናንተና እኔ ብቻ በአንድ ክፍል ውስጥ እንዳለን በማሰብ ለትንሽ ጊዜ ተመልከቱኝ።

እኔ እራሴ አይኖቻችሁን እያየሁና ስለ ምስክርነታችሁና ለእግዚአብሔር ስላላችሁ አምልኮ ይነግሩኛል ብዬ የማምናቸውን የተወሰኑ ጥያቄዎች መልሳችሁን በጥንቃቄ እያዳመጥኩኘ እንደሆነ አስባለሁ። ከ13 አመት በፊት ሚስዮኖችን የተናገርኳቸውን በሌላ መልክ ብናገር፣ አሁን የምንፈልገው በቤተክርስቲያኗ ታሪክ ውስጥ የሚስዮኖች ታላቅ ትውልድ ነው። ሙሉ ልባችሁንና መንፈሳችሁን እንፈልጋለን። ወጣት በዚህ ጊዜ የሚኖር የኋለኛ ቀን ቅዱስ በመሆን የእለት ተእለት የሙከራና የፈተና መንገዳችሁን ስታቀኑ፣ መንፈስ ቅዱስን የሚያዳምጡና ለሹክሹክታው መልስ መስጠት የሚያውቁ ጉልበት ያላቸው፣ የሚያስቡ፣ ፍቅር ያላቸው ሚስዮኖች እንፈልጋለን።

በሌላ አገላለፅ፣ ለሚስዮኖች ብቻ ሳይሆን ጨርሳችሁ ለተመለሳችሁትና ለመላ ትውልዳችሁ መስፈርቱን ከፍ የምናደርግበት ጊዜ ነው። ስለሆነም፣ እባካችሁን ለእነዚህ ጥያቄዎች መልሶቻችሁን በልባችሁ ውስጥ አሰላስሉት።

  1. ቅዱሳት መጽሐፍን በተደጋጋሚ ትመረምራለህን?

  2. በእያንዳንዱ ጠዋትና ማታ ከሰማይ አባትህ ጋር ለመነጋገር በፀሎት ትንበረከካለህን?

  3. ድሀ፣ ብዙ ለማበርከት የማትችል የተቸገረ ተማሪ ብትሆንም በእያንዳንዱ ወር ፆመህ የፆም በኩራቱን ታበረክታለህን?

  4. ቅዱስ ቁርባንን ለማዘጋጀት፣ ለመባረክ፣ ለማሳለፍ ስትጠየቅ ወይም ስትካፈል ስለ አዳኙና የሃጢያት ክፍያ ወስዋዕቱ በጥልቅ ታስባለህን?

  5. ስብሰባዎችህን ትካፈላለህን እና የሰንበትን ቀን ለመቀደስ ትጥራለህን?

  6. በቤት፣ በትምህርት ቤት፣ በቤተክርስቲያን እና በስራ ቦታዎች ታማኝ ነህን?

  7. በአስተሳሰብና በመንፈስ ንፁ ነህን? የራቁት ምስሎችን፣ ድረ ገፆችን፣ መፅሔቶችን፣ ፊልሞችን ወይም ፕሮግራሞችን፣ ቲንደርን ወይም ሰናፕቻት ፎቶዎችን ጨምሮ ስትመለከት ወላጆችህ፣ የቤተክርቲያን መሪዎችህ ወይም አዳኙ እራሱ ቢያዩክ የሚያሳፍርህን ነገሮች መመልከትን ታስወግዳለህን?

  8. የማይገቡ ቴክኖሎጂንና የመሃበረሰብ ሚዲያዎችን፣ መንፈሳዊነትህን የሚቀንሱ የቪዲዮ ጨዋታዎችንም ጨምሮ በማስወገድ በጊዜህ ጠንቃቃ ነህን?

  9. ከዛሬ ማታ ጀምሮ በሕይወትህ ውስጥ መቀየርና ማስተካከል ያለብክ ነገር አለን?

ለዚህ አጭር ግላዊ ጉብኝት አመሰግናለሁ። እያንዳንዱን እነዚህን ጥያቄዎች በሀቀኝነትና በማሰብ መልሳችኋል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። በየትኛውም እነዚህ መርሆች ላይ እራሳችሁን የጎደላችሁ ነገር እንዳለ ካገኛችሁ፣ በድፍረት ንስሃ እንድትገቡና ከፃድቅ የደቀመዝሙርነት የወንጌል ስነስርዓቶች ጋር እራሳችሁን እንድታዋህዱ እመክራችኋለሁ።

አሁን ወንድሞች፣ የወንጌልን ምስክርነት በልባችሁና ነፍሳችሁ ጠልቆ እንዲገባ የሚረዳችሁን ተጨማሪ ምክርችን ልስጣችሁን?

ጨርሳችሁ የተመለሳችሁትን ሚስዮኖች ለሕይወትና ቤተሰብ ለመመስረት የምታደርጉት ዝግጅት መቀጠል እንዳለበት ላስታውሳችሁ። “አር.ኤም” የሚሉት የእንግሊዝኛ ፊደላት ጡረታ የወጣ ሞርሞን ማለት አይደሉም! ጨርሶ እንደመጣ ሚስዮን “ሰዎች መልካም ስራን በጉጉት ማከናወን፣ እናም ብዙ ነገሮችን በራሳቸው ነፃ ምርጫ ማድረግ፣ እናም ብዙ ጽድቅንም መስራት አለባቸው።”2

እባካችሁን በሚስዮን ቦታ የተማራችሁትን ክህሎቶች በየቀኑ በዙሪያችሁ ያሉትን ሰዎች ሕይወት ለመባረክ ተጠቀሙበት። እይታቸውን በብዛት በትምህርት ቤት፣ በስራ ወይም በማህበራዊ እንቅስቃሴዎች ላይ የሚያተኩሩትን ከማገልገል እይታችሁን አታዙሩ። በአንፃሩ፣ በየቀኑ ቀጣይነት ያለው ለሌሎች አገልግሎት ለመስጠት በሚያስታውሳችሁና በሚያዘጋጃችሁ መንፈሳዊ ልማዶች ሕይወታችሁን አመጣጥኑ።

በሚስዮናችሁ ወቅት ሰዎችን በቤታቸው የመጎብኘትን ጠቃሚነት ተምራችኋል። ሁሉም የእኛ ወጣት ጎልማሶች የሙሉ ጊዜ ሚስዮን አገለገላችሁም አላገለገላችሁም ስለተመደባችሁ ብቻ ሳይሆን፣ ነገር ግን ለሰማይ አባትና ለልጆቹ ባላችሁ እውነተኛ ፍቅር ምክንያት ብቸኛ የሆኑ፣ የታመሙ ወይም ተስፋ የቆረጡ ሰዎችን የመጎብኘት ጠቀሜታን እንደምትረዱ ተስፋ አድርጋለሁ።

በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ያላችሁና ሚስዮን ለመሄድ እየተዘጋጃችሁ ያላችሁትን በሴሚነሪ ውስጥ እንድትሳተፉና እንድትመረቁ አበረታታችኋለሁ። እናንተ ወጣት ጎልማሶች በሐይማኖት ኢኒስቲትዩት ውስጥ መመዝገብ አለባችሁ።3 የቤተክርስቲያን ትምህርት ቤት ውስጥ እየተከታተላችሁ ከሆነ፣ በየሴሜስተሩ የሐይማኖት ትምህርት ውስጥ አንድ ክፍልን በተደጋጋሚነት ጨምሩ። በዚህ አስፈላጊ ጊዜ፣ እንደ ጎልማሳ ለሚስዮን ወይም ለዘላለም ጋብቻና ለሕይወታችሁ በምትዘጋጁበት ወቅት፣ ለመማርና ለማደግ እና የመንፈስ ቅዱስ መነሳሳትንና ምሪትን ለመቀበል መንገዶችን ለማግኘት መቀጠል አለባችሁ። በሴሚነሬ፣ በኢኒስቲትዩት ወይም በሐይማኖት ትምህርት ክፍሎች አማካኝነት ጠንቃቃ እና ፀሎታማ የሆነ የወንጌል ጥናት በዛ ግብ ውስጥ ይረዳችኋል።

የቤተክርስቲያን ትምህርት ቤት ተከታተላችሁም አልተከታተላችሁም፣ ኮሌጅ ተከታተላችሁም አልተከታተላችሁም፣ ወንጌልን ለማጥናት በጣም ጊዜ የለንም ብላችሁ አታስቡ። ሴሚነሪ፣ ኢንስቲትዩት ወይም የሐይማኖት ክፍሎች ለሕይወታችሁ መመጣጠን ይሰጧችኋል፣ እንዲሁም ቅዱሳት መጽሐፍንና የነብያትንና የሐዋርያትን ትምህርቶች በማጥናት ጊዜአችሁን የምታሳልፉበት ሌላ እድል በመስጠት አለማዊ ትምህርታችሁ ላይ ይጨምራሉ። እያንዳንዱ ወጣት ጎልማሳ እንዲያየውና እንዲካፈለው የማበረታታው አራት አዲስ ግሩም ኮርሶች አሉ።4

እናም በቅርንጫፋችሁ ውስጥ ወይም ባላገቡ ወጣት ጎልማሶች ዋርድ ወይም ካስማ ውስጥ የሚሰጠው ኢኒስቲትዩት ክፍሎችና እንቅስቃሴዎች በመንፈስ ስትማሩና ስታድጉ እንዲሁም እርስ በእርስ ስትተዋወቁ ከሌላ ወጣት ወንዶችና ሴቶቸች ጋር የምትሆኑበትና እርስ በራሳችሁ የምትደጋገፉበትና የምትነሳሱበት ቦታ እንደሚሆን አትርሱ። ወንድሞች፣ ሞባይላችሁን ብታስቀምጡና ትንሽ ዙሪያችሁን ብትመለከቱ፣ የወደፊት የዘላለም ጓደኛችሁን ልታገኙ እራሱ ትችላላችሁ።

ይመጣል ብላችሁ መዳወቃችሁት ወደልላው ምክሬ ይወስደኛል፥ ያላገቡ ወጣት ጎልማሶች የፍቅር ቀጠሮ ማድረግና ማግባት አለባቸው። እባካችሁን ወደኋላ ማዘግየታችሁን አቁሙ! አንዳንዶቻችሁ ቤተሰብ መመስረትን እንደምትፈሩ አውቃለሁ። ይሁን እንጂ፣ ትክክለኛውን ሰው በትክክለኛው ጊዜና በትክክለኛው ቦታ ካገባችሁ፣ መፍራት አይገባችሁም። በእርግጥ፣ የሚያጋጥማችሁ ብዙ ችግሮች በፅድቅ የፍቅር ቀጠሮ፣ መተጫጨትና ጋብቻ ላይ “በጉጉት ከተሰማራችሁ” ይወገዳሉ። በሞባይል መልእክት አትላክላት! በአካባቢህ ከሚገኙ ከጻድቅ የእግዚአብሔር ሴት ልጆች ሁሉ ጋር ድምጽህን ተጠቅመህ ራስህን አስተዋውቅ። የሰውን ድምጽ መስማቷ አስደንግጧት አዎን ልትልም ትችል ይሆናል።

የክህነት ወንድሞቼ፣ በሕይወታችን ውስጥ መስተካከል የሚፈልገውን ማንኛውን ነገሮች ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በሃጢያት ክፍያ መስዋዕቱ አማካኝነት እንደሚያስተካክለው እመሰክርላችኋሁ።

እሁድ ጠዋት ፋሲካን ለማክበር በምንዘጋጅበት በዚህ ምሽት፣ እባካችሁ የክርስቶስ የሃጢያት ክፍያ ስጦታን ለማስታወስ ከእኔ ጋር ቆም በሉ። የሰማይ አባታችንና አዳኛችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሻለ መንገድ እንደሚያውቋችሁና የበለጠ እንደሚወዷችሁ አስታውሱ።

በሃጢያት ክፍያው አማካኝነት ችግሮቻችንን፣ አዳኙ ህመሞቻችንንና ሃጢያቶቻቸችንን በራሱ ላይ ወሰደ። የአለም አዳኝ የፈራረሰ ተስፋችንን፣ ፈተናዎቻችንንና ሃዘኖቻችንን በመለማመድ በአትክልት ቦታውና በመስቀል ላይ በመሰቃየት እያንዳንዳችንን በግል ለመረዳት መጣ።5 እንደ አንድ የመጨረሻ የፍቅር ተምሳሌት ለእኛ ሞተ እና በዛ የዕጣ ፈንታው ምሽት በአዲስ መቃብር ተቀበረ።

በእሁድ ጠዋት ለእያንዳችን አዲስ ሕይወታን ቃል በመግባት ኢየሱስ ከሞት ተነሳ። የተነሳው ጌታ ከዛ ደቀመዛሙርቱን እያንዳንዳቸውን በክርስቶስ እምነት እንዲኖራቸው፣ ለሃጢያታቸው ንሰሃ እንዲገቡ፣ እንዲጠመቁ፣ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታን እንዲቀበሉና እስከመጨረሻው እንዲፀኑ እንዲያስተምሯቸው ስልጣን ሰጣቸው። ወንድሞች፣ እግዚአብሔር አባታችንና የተወደደው ልጁ ነብዩ ጆሴፍ ስሚዝን እንደጎበኙትና በእሱ አማካኝነት የኢየሱስ ክርስቶስን የወንጌል ሙላት እንደመለሱ እናውቃለን።

ወንድሞች ጠንካራ ሁኑ። የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት ጠብቁ። ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በፅድቅ ለመስራት የምንሻቸው ነገሮች በሙሉ የእኛ እንደሚሆኑ ቃል ገብቷል። የቤተክርስቲያን መሪዎች በእናንተ ላይ ተስፋ እያደረጉ ነው። እያንዳንዳችሁን ወጣት ጎልማሶች ወደፊት ለማጋባት፣ ለማገልገል እና ለመምራት እንድትዘጋጁ እንፈልጋለን፤ ለዚህም የምፀልየው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው፣ አሜን።