2010–2019 (እ.አ.አ)
ተማፅኖ ለእህቶቼ
ኦክተውበር 2015


ተማፅኖ ለእህቶቼ

ጥንካሬያችሁ፣ መለወጣችሁ፣ አቋማችሁ፣ የመምራት አቅማችሁ፣ ጥበባችሁና ድምፃችሁ ያስፈልገናል።

ውድ የቤተክርስቲያን ሽማግሌዎችራስባንድ፣ ሰቲቨንሰንእና ሬንላንድ፣ እኛ፣ የእናንተ ወንድሞች፣ ወደ አስራ ሁለቱ ሐዋርያት ጉባኤ እንኳን ደህና መጣችሁ እንላችኋለን። እኛ ካሁኑ እናንተን እና ውድ ዘለአለማዊ አጋሮቻችሁን እንወዳለን።

ወንድሞች እና እህቶች፣ ለአጠቃላይ ጉባኤ ከስድስት ወራት በፊት ስንገናኝ፣ በአጠቃላይ የቤተክርስቲያን ዋና መዋቅር ውስጥ ለውጥ የሚያመጡትን ለውጦች አልገመትንም። ሽማግሌ ኤል ቶም ፔሪ በጌታ እቅድ ውስጥ ስለ የማይቀየረው የጋብቻ እና የቤተሰብ ሚና ሀያል መልእክት አስተላልፈው ነበር። ከጥቂት ቀናት በኋላም፣ ከእኛ ስለሚነጥላቸው የካንሰር በሽታ ስንሰማ ድንግጥ ብለን ነበር።

የፕሬዘዳንት ቦይድ ኬ ፓከር ጤና እየደከመ ቢመጣም፣ በጌታ ስራ ውስጥ “ውትድርናውን” ቀጥለውበት ነበር። ያለፈው ሚዝያ እርሳቸው ደክምው ነበር፣ ቢሆንም ትንፋሻቸው እስካለች ጊዜ ድረስ ምስክረነትን ለማወጅ ወስነው ነበር። ከዛም፣ ከሽማግሌ ፔሪ ህልፈት ልክ ከ34 ቀናት በኋላ፣ ፕሬዘዳንት ፓከርም ማጋረጃውን ተሻገሩ።

በመጨረሻ አጠቃላይ ጉባኤአችን ሽማግሌ ሪቻርድ ጂ ስካትን አጣነው፣ ነገር ግን ስለአዳኙ የመሰከረውን ኃይለኛ ምስክርነት እናስታውሳለን። ከ12 ቀናት በፊት ሽማግሌ ስካት እቤት ተጠርቶ ውዱ ከሆነች ጀኒን ጋር በድጋሜ ተገናኝቶ ነበር።

ከመሞታቸው በፊት የፕሬዘዳንት ፓከር እና የሽማግሌ ስካት የቅርብ ቤተሰቦችን ጨምሮ በመጨረሻ ቀናቶቻቸው ወቅት ከእነዚህ ወንድሞች ጋር የመሆን እድሉን አግኝቼ ነበር። እነዚህ ሶስት ውድ ጓደኞች፣ እነዚህ ታላቅ የጌታ አገልጋዮች፣ በድንገት መለየታቸውን ለማመን ከብዶኝ ነበር። ከምናገረው በላይ እናፍቃቸዋለሁ።

በእነዚህ ያልተጠበቁ የክንውን ለውጦች ላይ ሳስብ፣ ከእኔ ጋር ከቆዩት ስሜቶች አንዱ በእነዚህ በሕይወት ያሉ ሚስቶች ውስጥ ያስተዋልኩት ነው። በባሎቻቸው አልጋ አቅራቢያ የሁለቱም ሴቶች፣እህት ዶና ስሚዝ ፓከር እና እህት ባርባራ ዴይቶን ፔሪ የነበራቸው በፍቅር፣ እውነት እና ንፁህ እምነት የመሞላት ሰላማዊ ምስል በአእምሮዬ የማይረሳ ሆኖ ተቀርፆ ነበር።

በመጨረሻ ሰኣታቸው ውስጥ እህት ፓከር ከባላቸው ጎን ተቀምጠው፣ ከመረዳት ሁሉ የሚልቀውን ያንን ሰላም ያንፀባርቁ ነበር።1 ለ70 አመታት በላይ ተወዳጅ አጋር የነበሩት በቅርቡ እንደሚለዩአቸው ቢያውቁም እንኳን፣ በእምነት የተሞላ ሴትን እርጋታ አሳዩ።ልክ በብሪንግሀም ሲቲ ቤተመቅደስ ቡራኬ ወቅት በተነሱት በዚህ ፎቶ ውስጥ እንደነበሩት፣ መልአክት ይመስሉ ነበር።

ምስል
ፕሬዘዳንት እና እህት ፓከር በብሪሀም ከተማ ዩታ ቤተመቅደስ

የዛ ተመሳሳይ አይነት ፍቅር እና እምነት ከእህት ፔሪ ሲመነጭ ተመለከትኩ። የእርሳቸው ለባላቸው እና ለጌታ መሰጠት ግልፅ ነበር፣ እና እኔን በጥልቅ ተሰማኝ።

ምስል
ሽማግሌ እና እህት ፔሪ

በባሎቻቸው የመጨረሻ ሰአታት፣ እና እስከ ዛሬም ድረስ በመቀጠል፣ እነዚህ ቆራጥ ሴቶች ቃል ኪዳን የሚጠብቁ ሴቶች የሚያንፀባርቁትን ጥንካሬ እና ብርታት አሳይተዋል።2 በቤተሰብ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ እንደ ሚስቶች፣ እናቶች እና አያቶች፤ እንደ እህቶች እና አክስቶች፣ እንደ መምህሮች እና መሪዎች፣ እና በተለይም እንደ ተምሳሌቶች እና የእምነት ጠባቂዎች ሁሌ እነዚህ ሴቶች ያላቸውን ተፅእኖ መመዘን ያማይቻል ነው።3

ከአዳም እና ሄዋን ጊዜያት ጀምሮ ባሉት በእያንዳንዱ የወንጌል ዘመናት ውስጥ ይሄ እውነት ነበር። ይሄ ዘመን ከሌሎቹ ሁሉ የተለየ በመሆኑ ምክንያት፣ የዚህ ዘመን ሴቶች ከሌሎች ዘመን ሴቶች ሁሉ የተለዩ ናቸው።4 ይሄ ልዩነት እድሎችን እና ሀላፊነቶችንም ጨምሮ ያመጣል።

ምስል
የፕሬዘዳንት ኪምቦል ገለፃ

ከሰላሳ ስድስት አመታት በፊት፣ በ1979፣ በጌታ ቤተክርስቲያን የወደፊት ሁኔታ ላይ ቃልኪዳን ጠባቂ ሴቶች ስለሚኖራቸው ተፅእኖ ፕሬዘዳንት ስፔንሰር ደብሊው ኪምቦል ጥልቅ ትንቢት ሰተው ነበር። እንዲህ በማለት ተነበዩ፣ “በዚህ የመጨረሻ ጊዜያት በቤተክርስቲያን አብዛኛው ዋና እድገቶች የሚመጡት በአለም መልካም ሴቶች በብዙ ቁጥር ወደ ቤተክርስቲያን ስለሚሳቡ ነው። ይህም የሚሆነው የቤተክርስቲያን ሴቶች በህይወታቸው በሚያንፀባርቁት የቅድስና እና ግልፅነት መጠን እና የቤተክርስቲያን ሴቶች፣ በደስታ መንገዶች፣ ከአለም ሴቶች ተለይተው በሚታዩበት መጠን ነው።”5

ውድ እህቶች፣ በዚህ የመቋጫ ወቅጥ የእኛ ወሳኝ አጋሮች የሆናችሁ፣ ፕሬዘዳንት ኪምቦል አስቀድመው የተመለከቱት ቀን ዛሬ ነው። እርሳቸው የተመለከቱት ሴቶች እናንተ ናችሁ! የእናንተ መልካምነት፣ ብርሀን፣ ፍቅር፣ እውቀት፣ ብርታት፣ ባህሪ፣ እምነት፣ እና የፅድቅ ህይወቶች የአለምን መልካም ሴቶች፣ ከነቤተሰቦቻቸው፣ በማይገለፅ ቁጥር ወደ ቤተክርስቲያን ይስባል።6

እኛ፣ የእናንተ ወንድሞች፣ የእናንተን ጥንካሬ፣ የእናንተን መለወጥ፣ የእናንተን ቁርጠኝነት፣ የእናንተን የመምራት አቅም፣ የእናንተን ጥበብ፣ እና የእናንተን ድምፆች እንፈልጋለን። ቅዱስ ቃልኪዳኖችን የሚገቡ፣ እና ከዛ የሚጠብቁ፣ በእግዚአብሔር ሀይል እና ስልጣን መናገር የሚችሉ ሴቶች በሌሉበት የእግዚአብሔር መንግስት ሙሉ አይደልም እና ሊሆንም አይችልም!7

ፕሬዘዳንት ፓከር እንዲህ አወጁ፤

“ዝግጁ የሆኑ ሴቶች እና ነገሮችን ማዋቀር የሚችሉ ሴቶች ያስፈልጉናል። ማቀድ እና መምራት እና ማስተዳደር የሚችሉ የማስፈፀም ብቃት ያላቸው ሴቶች ያስፈልጉናል፤ ማስተማር የሚችሉ ሴቶች፣ እራሳቸውን አውጥተው መናገር የሚችሉ ሴቶች። …

“የመረዳት ስጦታ ኖሯቸው በአለም ውስጥ ዝንባሌዎችን ማየት የሚችሉ እና ምንም ያህል ታዋቂ ቢሆኑም ግን ጥልቀት የሌላቸው እና አደገኛ የሆኑትን መለየት የሚችሉ ሴቶች ያስፈልጉናል።”8

ዛሬ፣ በእምነታቸው አስፈላጊ ነገሮች እንዲከሰቱ ማድረግ የሚችሉ እና በሀጢአት ህመም ውስጥ ባለች አለም የሰብአዊነት እና የቤተሰቦች ብርታት ያላቸው ጠባቂ የሆኑ ሴቶች እንደሚያስፈልጉን እኔ ልጨምር። በቃልኪዳን መንገድ ለእግዚአብሔር ልጆች እረኛ ለመሆን ቁርጠኝነት ያላቸው ሴቶች፤ የግል መገለጠን እንዴት መቀበል እንደሚችሉ የሚያውቁ ሴቶች፤ የቤተመቅደስ ቡራኬ ሀይልን እና ሰላምን የሚረዱ ሴቶች፤ ልጆችን እና ቤተሰቦችን ለመጠበቅ እና ለማጠንከር የሰማይ ሀይላት እንዴት እንደሚጠሩ የሚያውቁ ሴቶች፣ ያለፍራቻ የሚያስተምሩ ሴቶች ያስፈልጉናል።

በህይወቴ ሙሉ፣ በእነዚህ ሴቶች ተባርኬያለሁ። ያረፈችው ሚስቴ፣ ዳንዜል፣ እንደዚያ ያለች ሴት ነበረች። ልብ በመክፈት ቀዶ ህክምና የማስጀመር ጥረቶቼ ጨምሮ በሁሉም የህይወቴ መስኮች ስለነበራት ህይወት ቀያሪ ተፅእኖ እኔ ሁሌም አመስጋኝ ነኝ።

ከሀምሳ ስምንት አመታት በፊት፣ አብራ በተወለደችበት የልብ ከባድ በሽታ የተያዘች ትንሽ ልጅ ላይ ቀዶ ህክምና እንዳደርግ ተጠየኩ። በተመሳሳይ ሁኔታ ታላቅ ወንድሟ ሞቶ ነበር። ወላጆቿ ለእርዳታ ተማፀኑ። ስለውጤቱ አውንታዊ ስሜት አልነበረኝም ነገር ግን ህይወቷን ለማዳን የተቻለኝን ሁሉ ለማድረግ ቃል ገባሁ። የተቻለኝን ጥረት ባደርግም፣ ልጅቷ ሞተች። እነዚያው ወላጆች ቀጥለው 16 አመት ብቻ የሆናትን አሁንም ባልተስተካከለ ልብ የተወለደች ሌላ ልጃቸውን ይዘው ወደእኔ አመጡ። እንደገና፣ በእነሱ ጥያቄ መሰረት፣ ቀዶ ህክምናውን አደረኩ። ይህችም ልጅ ሞተች። ይሄ ልብ የሚሰብር በአንድ ቤተሰብ ውስጥ የሆነ ሶስተኛ ሞት እኔን እንዳልሆን አደረገኝ።

በሀዘን ተሞልቼ ወደቤት ሄድኩ። እራሴን በሳሎናችን ወለል ላይ ወረወርኩ እና ሌሊቱን ሙሉ አነባሁ። ዳንዜል በአጠገቤ ቆየች፣ ሁለተኛ የልብ ቀዶ ህክምና እነደማልሰራ በተደጋጋሚ ስናገር እየሰማች ነበር። ከዚያ፣ ጠዋት 11 ሰአት አከባቢ፣ ዳንዜል አየችኝና እንዲህ ብላ ጠየቀችኝ፣ “ለቅሶህን ጨረስክ? ልብስህን ልበስ። ወደ ቤተሙከራው እንደገና ሂድ። ወደ ስራ ሂድ! አሁን ስራ የምታቆም ከሆነ፣ አንተ እስካሁን ያወከውን ሌሎች በሚያም መልኩ ይግድ መማራቸው ነው።”

ኦ፣ የሚስቴ ምልከታ፣ ብርታት፣ እና ፍቅር ምነኛ ያስፈልገኝ ነበር! ወደ ስራ ተመለስኩ እና የበለጠ ተማርኩ። በዳንዜል የመነሳሳት ጉትጎታ ባይሆን ኖሮ፣ በልብ ቀዶ ህክምና አልገፋም ነበር እና በ1972 ውስጥ የፕሬዘዳንት ስፔንሰር ደብሊው ኪምባልን ህይወት ያዳነውን ቀዶ ህክምና ለማድረግ ዝግጁ አልሆንም ነበር።9

እህቶች፣ በመንፈስ በመመራት ወደ ልባችሁ እና አእምሯችሁ የሚመጡትን ነገሮች ስትናገሩ የእናንተን ተፅእኖ ስፋት እና ክልል ታስተውላላችሁ? በአንድ አስቸጋሪ ሁኔታ ሲነጋገሩ ስለነበረበት የካስማ ምክክር ስብሰባ አንድ ድንቅ የካስማ ፕሬዘዳንት ነገረኝ። የሆነ ወቅት፣ የካስማ ህፃናት ክፍል ፕሬዘዳንት እንዳልተናገረች ያስተወል እና የተሰማት ነገር እንዳለ ጠየቃት። “እንግዲያውስ፣ አለኝ፣” አለች እና የስብሰባውን አካሄድ በሙሉ የቀየረ ሀሳብ ማካፈሏን ተያያዘች። የካስማ ፕሬዘዳንቱ እንዲህ በማለት ቀጠለ፣ “እርሷ ስትናገር፣ እንደ መማክርት ስንሻው የነበረውን የመገለጥ ድምፅ እንደሰጠች መንፈስ ቅዱስ ለእኔ መሰከረ።

ውድ እህቶቼ፣ ጥሪያችሁ ምንም ይሁን፣ ሁኔታዎቻችሁ ምንም ይሁኑ፣ የእናንተ ስሜትን፣ የእናንተ መረዳትን፣ የእናነትን መነሳሳት እኛ እንፈልጋለን። በአጥቢያ እና የካስማ መማክርቶች ድምፃችሁን ከፍ እንድታደርጉ እና እንድታሰሙ እንፈልጋለን። ያገባችሁ እህቶች ሁሉ ቤተሰባችሁን በመምራት ከባላችሁ ጋር አንድ ስትሆኑ “አስተዋፅኦ እናዳላችሁ እና እንደ ሙሉ አጋር”10 እንድትናገሩ እንፈልጋለን። ያገባችሁ ወይም ያላገባችሁ ብትሆኑ፣ እናንተ እህቶች እንደ ስጦታ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት የተለዩ ችሎታዎች እና ልዩ የማስተዋል ብቃትን ተላብሳችኋል። እኛ ወንድሞች የእናንተን ልዩ አስተዋፅኦ ልናፈራ አንችልም።

የፍጥረት ሁሉ መቋጫ የሴት መፈጠር እንደሆነ እናውቃለን!11 ጥንካሬያቹን እንፈልገዋለን።

በቤተክርስቲያን፣ በአስተምሮቷ እና በህይወት አኗኗርችን ላይ ተቃውሞች እየጨመሩ ነው የሚመጡት። በዚህ ምክንያት፣ ስለ ክርስቶስ አስተምሮ ፅኑ መረዳት ያላቸው እና ያንን መረዳት በመጠቀም ሀጢአትን የሚቋቋም ትውልድ ለማፍራት የሚያስተምሩ እና የሚያግዙ ሴቶች ያስፈልጉናል።12 ማታለልን ከነሙሉ ቅርፁ ለይተው ማወቅ የሚችሉ ሴቶች ያስፈልጉናል። እግዚአብሔር ለቃልኪዳን ጠባቂዎች የሚያዘጋጀው ሀይል እንዴት እንደሚገኝ የሚያውቁ እና እምነቶቻቸውን በራስ መተማመን እና በልግስና የሚገልፁ ሴቶች ያስፈልጉናል። የእናታችን ሔዋን ብርታት እና ራእይ ያላቸው ሴቶች ያስፈልጉናል።

ውድ እህቶቼ፣ ለእናንተ ዘለአለማዊ ህይወት የሚሆን ከመለወጣችሁ በላይ የሆነ ምንም ወሳኝ ነገር የለም። በተበላሸ አለም ውስጥ የፅድቅ ህይወታቸው ገኖ የሚታየው የተለወጡ፣ የቃልኪዳን ጠባቂ ሴቶች ናቸው--እናም የእኔን ውድ አጋር ዌንዲን ያካትታል--- እና ስለሆነም በአስደሳች መንገዶች ልዩ ሆነው ይታያሉ።

ስለዚህ ዛሬ፣ ወደፊት እንዲራመዱ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን እህቶቼን እማፀናለሁ። ቤታችሁ፣ በማህበረሰባችሁ፣ እና በእግዚአብሔር መንግስት ውስጥ ከዚህ በፊት ከኖራችሁ በላይ፣ ትክክለኛውን እና ተፈላጊውን ቦታችሁን ያዙ። የፕሬዘዳንት ኪምቦልን ትንቢት እንድታሳኩ እማፀናችኋለሁ። እና ያንን ስታደርጉ፣ አስተዋፅኦችሁን በማይገለፅ መንገድ መንፈስ ቅዱስ እንደሚያጎላው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ቃል እገባላችኋለሁ።

የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን እውነታ እና የእርሱን የቤዛነት፣ የሀጢአት ከፋይ፣ እና የፃዲቅነት ሀይል እመሰክራለሁ። እና፣ እንደ አንዱ የእርሱ ሐዋርያ፣ ውድ እህቶች አመሰግናችኋለሁ፣ እና በዚህ ፃዲቅ ስራ ውስጥ እጅ ለእጅ ተያይዘን ስንጓዝ፣ ወደ ሙሉ ማእረጋችሁ ከፍ እንድትሉ፣ የፍጥረታችሁን ሚዛን እንድታሟሉ እኔ እባርካችኋለሁ። በአንድነት፣ አለምን ለጌታ ዳግም ምፅአቱ በማዘጋጀቱ እናግዛለን። እንደ ወንድማችሁ፣ ስለዚህ እመሰክራለሁ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።

ማስታወሻዎች

  1. ፊልጵስዮስ 4፥7 ተመልከቱ።

  2. ይህ ትዕዛዛትን በመጠበቅ የምንወዳቸው ሰዎች ከዚህ ህይወት ሲመረቁ የለቅሶ እንባን ያካትታል(D&C 42:45 ተመልከቱ)።

  3. በይስሀቅ እና በልጃቸው ያዕቆብ ላይ የነበረውን የርብቃ ተፅዕኖ በዘፍጥረት 27፥4628፥1–4 ውስጥ ተመልከቱ።

  4. ጆሴፍ ፊልዲንግ ስሚዝ፣ Answers to Gospel Questions ፣በጆሴፍ ፊልዲንግ ስሚዝ፣ ዳግማዊ የተደራጀ፣ 5 vols. (1957–66)፣ 4:166 ተመልከቱ። እባካችሁ አትኩሩበት፥ የድሮው ዘመናት በአለም ትንሽ ክፍል ላይ የተገደቡ ነበሩ እናም በክህደት ተፈጽመው ነበር። ከዚህ በሚያነጻጽር፣ ይህ ዘመን በቦታ ወይም በጊዜ የተገደበ አይደለም። አለምን ይሞላል እናም ከጌታ ዳግም ምፅዓት ጋር ይደባለቃል።

  5. Teachings of Presidents of the Church: Spencer W. Kimball (2006), 222–23።

  6. በተወለድኩበት ጊዜ፣ ከ600 ሺህ በታች የሆኑ የቤተክርስቲያን አባላት ነበሩ። ዛሬ ከ15 ሚልዮን በላይ ናቸው። ያም ቁጥር በማደግ ይቀጥላል።

  7. ፕሬዘደንት ጆሴፍ ፊልዲንግ ስሚዝ ለሴቶች መረዳጃ ማህበር እህቶች ይህን ነገሯቸው፣ “በስልጣን ለመናገር ትችላላችሁ፣ ምክንያቱም ጌታ በእናንተ ላይ ስልጣን አሳርፏልና።” ደግመውም እንዲህ ብለዋል የሴቶች መረዳጃ ማህበር “ብዙ ታላቅ ነገሮች ለማድረግ ሀይል እና ስልጣን ተሰጥቷቸዋል። የሚያደርጉት ስራ የሚከናወነው በመለኮታዊ ስልጣን ነው” (“Relief Society—an Aid to the Priesthood,”Relief Society Magazine, Jan. 1959, 4, 5)። እነዚህ ጥቅሰቶች በሽማግሌ ዳለን ኤች ኦክስ በጉባኤ ንግግር፣ “The Keys and Authority of the Priesthood፣” Liahona፣ ግንቦት 2014፣ 51 ተጠቅሰው ነበር።

  8. ቦይድ ኬ. ፓከር፣ “The Relief Society፣” Ensign፣ ህዳር 1978፣ 8፤ ደግሞም ኤም. ራስል ባለርድ፣ Counseling with Our Councils: Learning to Minister Together in the Church and in the Family (1997), 93 ተመልከቱ።

  9. ስፔንሰር ጄ. ኮንዲ፣ ራስል ኤም. ኔልሰን፣Prophet, Surgeon, Apostle (2003)፣ 146፣ 153–56 ተመልከቱ። ማስታወሻ፥ በ1964 (እ.አ.አ) ፕሬዘደንት ኪምባል እኔን እንደ ካስማ ፕሬዘደንት ሾሙኝ እናም በልብ ኦፕራስዮን አዲስ ዘዴ በምደርግበት ህይወታቸው የሚተርፍ ሰው ቁጥር እንደሚጨምር በረከት ሰጡኝ። ከስምንት አመት በኋላ ይህን የልብ ኦፕራሲዮን ዘዴ በፕሬዘደንት ኪምብል ላይ እንደምጠቀም ሁለታችንም አላወቅንም ነበር።

  10. ስለጋብቻ እንደ ትብብር በምንናገርበት ጊዜ፣ ጋብቻን እነ ሙሉ መተባበሪያ እንነጋገርበት። የኋለኛው ቀን ቅዱሳን ሴቶቻችን በዚያ ዘለአለማዊ መደብ ውስጥ ጸጥተኛ ተባባሪ ወይም የተገደቡ ተባባሪዎች እንዲሆኑ አንፈልግም!” እባካችሁን አስተዋጽኦ እናም ሙሉ ትብብር አድርጉ”( ስፔንሰር ደብሊው. ኪምባል፣ “Privileges and Responsibilities of Sisters፣” Ensign፣ ህዳር 1978፣ 106)።

  11. “የአለም እቅዶች በሙሉ እንድ በአለም ውስጥ ያሉት በሙሉ፣ በክህነት ፍጥረት ውስጥ እንደ ዋና መካከለኛ ድንጋይ እንደሆኑት፣ ያለሴት ምንም እንዳልሆነ ይሆናሉ” (ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “Lessons from Eve፣” Ensign፣ ህዳር 1987፣ 87)። “ሔዋን የእግዚአብሔር የመጨረሻ ፍጥረት፣ ከዚያ በፊት ከነበሩት ታላቅ ስራዎች ታላቋ መፈጸሚያ ሆነች” (ጎርደን ቢ. ሒንክሊ፣ “The Women in Our Lives፣” Liahona፣ ህዳር 2004፣ 83)።

  12. ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “Children of the Covenant፣” Ensign፣ ግንቦት 1995፣ 33 ተመልከቱ።