2010–2019 (እ.አ.አ)
እምነት በእድል አይደለም፣ ግን በምርጫ ነው
ኦክተውበር 2015


እምነት በእድል አይደለም፣ ግን በምርጫ ነው

እምነት በኢየሲስ ክርስቶስ እኛ ለማመን ስንመርጥ እና ስንሻው እና ስንይዘው የሚመጣ የሰማይ ስጦታ ነው።

አዳኝ በዙሪያው የነበሩትን ሰዎች የእምነት ጥንካሬ ወይም ድክመት ያውቅ ነበር። ለአንዷ፣ እንዲህ አላት፣ “እምነትሽ ታላቅ ነው።”1 ለሌላ ደግሞ እንዲህ ብሎ አረዳ፣ “እናንተ እምነት የጎደላችሁ።”2 ሌሎችን ጠየቀ፣ “እምነታችሁ የት ነው?”3 እና ኢየሱስ ሌላውን እንዲህ በማለት ለየ፣ “በእስራኤል ሁሉ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም።”4

እራሴን እንዲህ ብዬ እጠይቃለሁ፣ “አዳኝ እምነቴን እንዴት ነው የሚያየው?” እና ዛሬ ምሽት እናንተን እጠይቃለሁ፣ “አዳኝ እምነታችሁን የሚያየው እንዴት ነው?”

በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ማመን፣ በአየር ላይ እንደሚንሳፈፍ፣ በጣም ቀላል የሆነ ነገር አይደለም። እምነት በድንገት እኛ ላይ የሚወድቅ አይደለም፣ ወይም በመወለድ መብት ከእኛ ጋር የሚቆይ አይደለም። ቅዱሳን መጽሐፍት እንደሚሉት፣ “ስለማናየው ነገር የሚያስረዳ...”5 ነው። እምነት መንፈሳዊ ብርሀንን ይረጫል፣ እናም ያ ብርሀን የሚለይ ነው።6 እምነት በኢየሱስ ክርስቶስ ለማመን7 ስንመርጥ እና ስንሻው እና ስንይዘው ከሰማይ የሚመጣ ስጦታ ነው። እምነታችሁ ወይ በጥንካሬ እያደገ ነው ወይም እየደከመ ነው። እምነት በዚህ ህይወት ብቻ የሚያስፈልግ ሳይሆን፣ ነገር ግን ከመጋረጃው በላይ ባለን እድገትም የሚስፈልግ የሀይል መርህ ነው።8 በክርስቶስ ጸጋ፣ በእርሱ ስም በማመን ምክንያት አንድ ቀን እንድናለን።9 የወደፊት እምነታችሁ በእድል አይደለም፣ ግን በምርጫ ነው።

የአንድ ወጣት ብራዚላዊ እምነት

ከወር በፊት በብራዚል ውስጥ አሮልዶ ካቫልቻንትን አገኘሁት። በ21 አመቱ ነበር የተጠመቀው፣ በቤተሰቡ ውስጥ የመጀመሪያው የቤተክርስቲያን አባል ነበር። እምነቱ በጉልህ በራ፣ እናም ወዲያውኑ ሚስኦን ለማገልገል መዘጋጀት ጀመረ። በአሳኝ ሁኔታ፣ የአሮልዶ እናት ካንሰር እንዳለባት ታወቀ። ከሶስት ወራት በኋላ፣ ከመሞቷ በፊት በነበሩት ብቸኛ ቀናት፣ በጣም ስለሚያሳስባት ነገር ለአሮልዶ ነገረችው፤የሚረዱ ዘመዶች አልነበራቸውም። አሮልዶ ለሁለቱ ታናሽ እህቶቹ እና ታናሽ ወንድሙ ሙሉ ሀላፊነት መውሰድ ነበረበት። እርሱም በእርጋታ በሞት መንገድ ላይ ላለችው እናቱ ቃል ገባ።

ምስል
የካቫልቻንት እህቶች እና ወንድም

በቀን ባንክ ውስጥ የሰራል፣ እና ማታ ዩኒቨርስቲ ይከታተላል። የጥምቀት ቃልኪዳኑን መጠበቁን ቀጠለ፣ ነገር ግን የሙሉ ጊዜ ሚስኦናዊ የመሆን ተስፋው ጠፋ። ተልእኮው ቤተሰቡን መንከባከብ ሆነ።

ከወራት በኋላ የቅዱስ ቁርባን ስብሰባ ንግግሩን ሲያዘጋጅ፣ ሳሙኤል ለንጉስ ሳኦል የተናገረውን ቃላት አሮልዶ አጠና፤ “መታዘዝ ከመሰዋት ይበልጣል።”10 ሚስኦን ለማገልገል ከነብይ የመጣውን ጥሪ መታዘዝ እንደሚገባው አሮልዶ ሊሆን የማይችል የሚመስል ስሜትን ተቀበለ። ከፊቱ በነበሩት እንቅፋቶች ተስፋ ሳይቆርጥ፣ በታላቅ እምነት ወደ ፊት ተጓዘ።

ምስል
ኤልደር አሮልዶ ካቫልቻንት

አሮልዶ የቻለውን የብራዚል ገንዘብ ሁሉ አጠራቀመ። 23 አመቱ ላይ፣ የሚስኦን ጥሪውን ተቀበለ። ካጠራቀመው ላይ በየወሩ ለቤተሰቡ ምን ያህል ማውጣት እንዳለበት ለወንድሙ ነገረው። የሚስኦኑን እና የወንድም እና እህቶቹን ሙሉ ወጪ ለመክፈል አሮልዶ አሁንም በቂ ገንዘብ አልነበረውም፣ ነገር ግን በእምነት ወደ ኤምቲሲ ገባ። ከሳምንት በኋላ ከብዙዎቹ በረከቶቹ አንዱን አገኘ። ኤልደር ካቫልቻንትን ቀጥሮት የነበረው ባንክ ሊቀበል የነበረውን የመጨረሻ ስራው ክፍያውን እጥፍ አደረገለት። ይሄ ተአምር፣ ከሌሎች መካከል፣ ለሚስኦኑ እና በሌለበት ቤተሰቡ ለሚጠቀሙበት ወጪ የሚያስፈልገውን ገቢ አስገኘ።

ምስል
የካቫልቻንት ቤተሰብ በአሁን ወቅት

ከሀያ አመታት በኋላ፣ ወንድም ካቫልቻንት አሁን በረሲፍ ብራዚል ቦ ቪያግም ካስማ ውስጥ በፕሬዘዳንትነት እያገለገለ ነው። ወደኋላ ሲያስብ፣ ስለእነዚያ ቀናት እንዲህ ይላል፣ “በፅድቅ ለመኖር ስሞክር፣ የአዳኝን ፍቅር እና ምሬት ተሰምቶኛል። ብዙ ችግሮችን እንዳልፍ በማድረግ፣ እምነቴ አድጓል።”11 የአሮልዶ እምነት በእድል የመጣ አይደለም፣ ግን በምርጫ ነው።

ለጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጥልቅ እምነት ያላቸው ብዙ ክርስቲያን ወንዶች እና ሴቶች አሉ፣ እናም እኛ እናከብራቸዋለን።

ከእግዲህ በገለልተኛ ቦታ ላይ አለመሆን

ነገር ግን ወንድሞች፣ እኛ የበለጠ ነገር ተሰቶናል፤ በቅዱስ መላእክት ወደ ምድር የተመለሰው የእግዚአብሔር ሀይል የሆነው፣ የእግዚአብሔር ክህነት። ይሄ እናንተን ልዩ ያደርጋችኋል። ከእንግዲህ በገለልተኛ ቦታ ላይ አትቆሙም። እምነታችሁ የሚያድገው በእድል አይደለም፣ ግን በምርጫ ነው።

ህይወታችንን የምንኖርበት መንገድ እምነታችንን ይጨምራል ወይም ይቀንሳል። ጸሎት፣ መታዘዝ፣ ታማኝነት፣ የአስተሳሰብ እና ድርጊት ንፅህና፣ እና እራስ ወዳድ አለመሆን እምነትን ይጨምራሉ። ያለ እነዚህ ነገሮች፣ እምነት ይቀንሳል። አዳኝ ለጴጥሮስ እንዲህ ያለው ለምን ነበር?፣ “እምነትህ እንዳይጠፋ ለአንተ እማልዳለሁ።”12 ምክንያቱም እምነታችንን በማጥፋት የሚደሰት ጠላት አለ! እምነታችሁን በመጠበቅ ውስጥ ጽኑ።

ታማኝ ጥያቄዎች

ታማኝ ጥያቄዎችን ማቅረብ እምነትን የመገንባት አስፈላጊው ክፍል ነው፣ እናም እውቀታችንን እናም ስሜቶቻችንንም እንጠቀማለን። ጌታ እንዲህ አለ፣ “በአእምሮአችሁ እና በልባችሁ ውስጥ እነግራችኋለሁ።”13 ሁሉም ምላሾች ወዲያው አይመጡም፣ ነገር ግን አብዛኛው ጥያቄዎች ከልብ በሆነ ጥናት እና ምላሾችን ከእግዚአብሔር በመሻት ሊመለሱ ይችላሉ። ያለ ልባችን አእምሮአችንን መጠቀም መንፈሳዊ ምላሾችን አያመጣም። “ከእግዚአብሔር መንፈስ በቀር ለእግዚአብሔር ያለውን ማንም አያውቅም።”14 እናም እኛን ለመርዳት፣ኢየሱስ “ሌላ አጽናኝ… የእውነት መንፈስ”ን ቃል ገብቶልናል።15

እምነት ለእያንዳንዱ ጥያቄ ምላሽን አይጠብቅም። ነገር ግን፣ “ሁሉንም ነገር አላውቅም፣ ግን በደቀመዛሙርነት መንገድ ለመቀጠል በቂ አውቃለሁ” ብለን አንዳንዴ እናስብ። እምነት ወደፊት ለመጓዝ ማረጋገጫን እና ብርታትን ይሻል።16

እምነት በሌላቸው ሰዎች በሚሰጡ ምላሾች በመቀጣጠል፣ እራስን በፅኑ ጥርጣሬ ውስጥ ማስመጥ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ እና በተመለሰው ወንጌላይ ላይ ያለን እምነት ያዳክማል።17 “ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም።”18

ለምሳሌ፣ ነብዩ ዮሴፍ ስሚዝን አስመልክቶ ያሉት ጥያቄዎች አዲስ አይደሉም። ይሄ ስራ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በእርሱ ላይ በተቃዋሚዎቹ ሲዘነዘሩ ነበር። በእምነት ለሆኑ ሰዎች፣ ክስተቶችን ወይም 200 አመታት አከባቢ የሆነውን የነብዩ ዮሴፍ አርፍተ ነገሮችን በ21ኛው ክፍለ ዘመን የተቀለሙ መነፅሮች ውስጥ በመመልከት በታማኝነት ለሚጠይቁ፣ ጓደኛዊ ምክርን ላካፍል፤ ለጊዜው፣ ለወንድም ዮሴፍ እረፍት እንስጠው! ለወደፊቱ፣ በአሁኑ ጊዜ ካለው የኢንተርኔት ዳሰሳ በ100 እጥፍ የበለጠ መረጃ ይኖራችኋል፣ እናም በትክክል የሚያስተማምን ይሆናል።19 የዮሴፍን ህይወት አጠቃላችሁ አስቡት--በድህነት ውስጥ ተወልዶ እና ጥቂት ትምህርት አግኝቶ፣ ግን እርሱ መጽሐፈ ሞርሞንን 90 ቀናት ባነሰ ጊዜ ተረጎመው።20 አስር ሺዎች የሚቆጠሩ ታማኝ፣ ቁርጠኛ ወንዶች እና ሴቶችን በዳግም መመለስ ምክንያት ተደስተዋል ፣ በ38 አመቱ ዮሴፍ ምስክርነቱን በደሙ አትሟል። ዮሴፍ ስሚዝ የእግዚአብሔር ነብይ እንደነበር እመሰክራለሁ። ይህንን በአእምሮአችሁ አኑሩ፣ እና ወደፊት ተጓዙ!

እምነታችንን የሚያሳድጉ ስጦታዎች

ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን፣ የእግዚአብሔር ልጅም እንደሆነ ፍፁም ማረጋገጫ የሚሰጡ መጽሐፍ ቅዱስ እና መጽሐፈ ሞርሞን አሉን። ጆህን ቴይለር ስራውን በ1852 በፈረንሳይ ሲጀምር ያሳተመውን የፈረንሳየኛ መጽሐፈ ሞርሞን የመጀመሪያ ቅጂ በእጄ ይዣለሁ። አሁን መጽሐፈ ሞርሞን በሙሉ ወይም በከፊል በ110 ቋንቋዎች በአለም ዙሪያ ይገኛል። የዳግም መመለስ እውነታን መንፈሳዊ እና ተጨባጭ ምስክርነትን ያቀርባል። መጽሐፈ ሞርሞንን ለመጨረሻ ጊዜ ከጫፍ እስከ ጫፍ ያነበባችሁት መቼ ነበር? ደግማችሁ አንብቡት። እምነታችሁን ይጨምራል።21

እምነታችንን የሚያሳድገው ሌላው የእግዚአብሔር ስጦታ የቀዳሚ አመራር እና የአስራ ሁለቱ ሐዋርያት ጉባኤ ምሬት ነው። ዛሬ ሶስት አዲስ አባላትን ወደአስራ ሁለቱ እንዲሆኑ ድጋፍ ሰተናል፣ እናም እንኳን ደህና መጣቸሁ እላቸዋለሁ። ጳውሎስ እንዲህ አለ፤

“ሐዋርያትን፣ እና…ነብያትን ጠራ፤

“ቅዱሳንን ለማነፅ…

“ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ…ወደሚገኝ አንድነት እስክንደርስ..

“ከእንግዲህም… እንደ ስህተት ሽንገላ ባለ ተንኮል በሰዎችም ማታለል ምክንያት በትምህርት ነፋስ ሁሉ ወዲያና እና ወዲህም እንዳንንሳፈፍ።”22

የቀዳሚ አመራር እና አስራ ሁለቱ ሐዋርያት ምሬት እምነታችንን ለመጠበቅ ይረዳል።

ምስል
የእምነት ነበልባሎች

የእምነታችሁ መነሻ እሳት ትንሽ ቢሆንም እንኳን፣ ጻዲቅ ምርጫዎች፣ ታላቅ በእግዚአብሔር መተማመንን ያመጣሉ፣ እናም እምነታችሁ ይጨምራል። የስጋዊነት ችግሮች በእናንተ ላይ ይነፍሳሉ፣ እና በጨለማ ውስጥ የክፉ ሀይሎች ያደፍጣሉ፣ እምነታችሁን ለማጥፋት ተስፋ በማድረግ። ነገር ግን መልካም ምርጫዎችን በማድረግ ስትቀጥሉ፣ በእግዚአብሔር ላይ ስትታመኑ እና ልጁን ስትከተሉ፣ ጌታ የበዛ ብርሀን እና እውቀት ይልካል፣ እናም እምነታችሁ የጸና እና የማይነቃነቅም ይሆናል። ፕሬዘዳንት ቶማስ ኤስ ሞንሰን እንዳሉት፣ “አትፍሩ…የወደፊቱ እንደ እምነታችሁ ሁሉ ብሩህ ነው።”23

ፖርተር፣ ዜን፣ እና ኦፕንሾ

የዚህች ቤተክርስቲያን ወጣት ወንዶች አምነት የሚያስደንቅ ነው!

ምስል
የኦፐንሾ ቤተሰብ

በዚህ አመት ሰኔ 12 ላይ፣ በዩታህ አጥቢያ የነበሩት ኤጲስ ቆጶስ፣ ባለቤታቸው እና ሁለት ልጆቻቸው በአውሮፕላን አደጋ ስለመሞታቸው የሚያትት ኢሜል ደረሰኝ። አውሮፕላኑ ጥቂት የአየር ክልል እንደገባ፣ ድንገት ሀይሉ ጠፍቶ ከመሬት ጋር ሲጋጭ አብራሪው ኤጲስ ቆጶስ ማርክ ኦፕንሾ ነበሩ። ኤጲስ ቆጶስ ኦፕንሾ፣ ባለቤታቸው ኤሚ እና ልጆቻቸው ታነር እና ኤሊ በዚያ አደጋ ሞቱ። ተአምር በሆነ መልኩ፣ የአምስት አመት ልጃቸው ማክስ፣ በአውሮፕላኑ መቀመጫ ወደ ውጪ በመወርወሩ፣ የተሰበሩ አጥንቶች ኖሮት ተረፈ።

ልጃቸው ኤልደር ፖርተር ኦፕንሾ በማርሻል አይላንድ ማጁሮ ሚስኦን ውስጥ እያገለገለ እንደነበር እና የ17 አመት ልጃቸው ዜን፣ ለትምህርት የባህል ልውውጥ ጀርመን እንደነበር ሰማሁ።

በክሪስማስ አይላንድ ለነበረው ኤልደር ኦፕንሾ ደወልኩ። በእናቱ፣ አባቱ፣ ወንድም እና እህቱ ድንገተኛ ሞት ልቡ ቢሰበርም፣ የኤልደር ኦፕንሾ ትኩረት ወዲያው ወደ ሁለቱ ታናናሽ ወንድሞቹ ሆነ።

በስተመጨረሻ ኤልደር ኦፕን ሾ እና ወንድሙ ዜን ሌሎቹ በቤት ውስጥ መርዳት እንደሚችሉ እና ፖርተር በሚስኦኑ መቆየት እንዳለበት ወሰኑ። ወላጆቻቸው የሚፈልጉት ያንን እንደሚሆን አውቀው ነበር።

ምስል
ኤልደር ፖርተር ኦፕንሾ በጥምቀት ወቅት

ከኤልደር ኦፕንሾ ጋር ሳወራ፣ ሀዘኑ ብቻ ሳይሆን የእምነቱ እሳትም ተሰማኝ። “በራስ መተማመኑ አለኝ፣እናም ቤተሰቤን ደግሜ እንደማያቸው ያለ ምንም ጥርጣሬ አውቃለሁ።…በፈተናዎች ውስጥ ጥንካሬ ሁሌም የሚገኘው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ ነው…በዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እኔን እና ወንድሞቼን በመርዳት የእግዚአብሔር ሁሉን ቻይ እጆች በጣም በግልፅ ታይተዋል።”24

ምስል
ዜን ኦፕንሾ በቀብር ወቅት ንግግር ሲሰጥ

በቀብር ላይ ዜንን ለመጀመሪያ ጊዜ አገኘሁት። በቤተክርስቲያን ውስጥ ከፊታችን የነበሩትን አራት የእሬሳ ሳጥኖች ስመለከት፣ የ17 አመቱ ልጅ ንግግር ሲያደርግ በነበረው እምነት ተደነኩ። እንደዚህ አለ “ዛሬ፣ የእናቴን፣ አባቴን፣ ታነርን እና ኤሊን ህይወት ለማሰብ በትሁት ልቦች እና ደካማ ነብሳት ተሰብስበናል… አብረን አውርተናል፣ አብረን አልቅሰናል፣ አብረን አስታውሰናል፣ እናም የእግዚአብሔር እጅ በአንድነት ተሰምቶናል።…

“የአደጋውን ዜና ከሰማሁ ቀን በኋላ፣ ከእናቴ የሆነ ደብዳቤ በቦርሳዬ ውስጥ አገኘሁ። በደብዳቤው እንዲህ ብላ ጽፋለች፤ ‘ዜን፣ ማን እንደሆንክ እና ከየት እንደመጣህ አስታውስ። ለአንተ እንፀልይልሀለን እናም ትናፍቀናለህ።’በማለት ዜን ቀጠለ፤ “ከእናቴ ከዚህ ይበልጥ በቂ የሆነ የመጨረሻ ቃላት ሊኖር አይችልም። እርሷ፣ ከታነር፣ ኤሊ እና ከአባቴ ጋር ለወንድሞቼ እና ለእኔ እየፀለዩ እንደሆነ አውቃለሁ። እኔ ማን እንደሆንኩ እንዳስታውስ እንደሚፀልዩ አውቃለሁ፣ ምክንያቱም እኔ ልክ እንደእናንተ፣ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ፣ እናም እርሱ ወደእዚህ ልኮኛል። ምንም ያህል ብቸኝነት ቢሰማን፣ እግዚአብሔር እንደማይተወን እመሰክራለሁ።”25

ውድ ጓደኞቼ፣ እምነታችሁ ስትወለዱ የጀመረ አይደለም፣ እናም በሞትም የሚያበቃ አይደለም። እምነት ምርጫ ነው። እምነታችሁን አጠንክሩ፣ እና የጌታ አረጋጋጭ ቃላት እንዲገቧችሁ ኑሩ፤ “እምነታችሁ ታላቅ ነው።” ይህንን ስታደርጉ፣ እምነታችሁ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ አማካኝነት፣ አንድ ቀን በእግዚአብሔር እይታ ውስጥ ንጹህ ሆናችሁ ከምትወዷቸው ጋር እንድትቆሙ እንደሚያደርግ ቃል እገባላችኋለሁ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን ።

ማስታወሻዎች

  1. ማቴዎስ 15፥28

  2. ማቴዎስ 6፥30

  3. ሉቃስ 8፥25

  4. ማቴዎስ 8፥10

  5. ዕብራውያን 11፥1

  6. አልማ 32፥35 ተመልከቱ።

  7. See L. Whitney Clayton, “Choose to Believe,” Liahona, May 2015, 36–39.

  8. Lectures on Faith (1985), 3።

  9. ኤፌሶን 2፥8 ተመልከቱ።

  10. 1 ሳሙኤል 15፥22

  11. አርኖልድ ቻካልቻንቴ ወንድሞቹን እና እህቶቹን ለመንከባከብ ለእናቱ ቃል የገባበት ታሪክ ውስጥ ተጨማሪ ታሪክ አለ። ከእናቱ ሞት በኋላ፣ ወንድሞቹን እና እህቶቹን “ልጆቼ” ብሎ ይጠራቸው ነበር። በሚስዮኑ ጊዜ፣ በገና እና በእናት ቀን ስልክ በሚደውልበት ጊዜ የሚነጋገርባቸው ስለእያንዳንዱ የቤተሰብ አባላት ፈተናዎችን በሚመለከት ነበር። በሚስዮኑ በኋላ በታላቅ መስዋዕት፣ አርኖልድ ለትምህርታቸው እና ለወንድሙ ሚስዮን የገንዘብ ሀላፊነትን ወሰደ። አርኖልድ በ32 አመቱ ያገባው እስቶቹና ወንድሙ ካገቡ በኋላ ነበር። አሁንም ቅርብ የሆኑ ቤተሰቦች ናቸው።

  12. ሉቃስ 22፥32

  13. ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 8፥2

  14. 1 ቆሮንቶስ 2፥11

  15. ዮሀንስ 14፥16–17

  16. Adam Kotter, “When Doubts and Questions Arise,” Liahona, Mar. 2015, 39–41 ተመልከቱ።

  17. ሽማግሌ ኒል ኤ. ማክስዌል አንዴ እንዳሉት፣ “አንዳንዶች፣ ልክ ኢየሱስን ለመረዳት ይሁዳን እንደማነጋገር አይነት፣ ቤተክርስቲያኗን በከዷት ሰዎች አስተያየት ብቻ ለማጥናት ይፈልጋሉ። የከዱ ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ የሚነግሩን ስለራሳቸው እንዲ ትተውት ስለወጡት አይደለም” (“All Hell Is Moved” [Brigham Young University devotional, Nov. 8, 1977], 3, speeches.byu.edu)

  18. 1 ቆሮንቶስ 2፥17

  19. “ፍጹም ነኝ ብዬ በምንም አልነገርኳችሁም፤ ነገር ግን ባስተማርኩት ራዕያት ውስጥ፡ምንም ስህተቶች የሉም” (Teachings of Presidents of the Church: Joseph Smith [2007], 522)።

  20. W. Welch and Tim Rathbone, “The Translation of the Book of Mormon: Basic Historical Information” (Foundation for Ancient Research and Mormon Studies, 1986) ተመልከቱ።

  21. የመፅሐፈ ሞርሞን መንፈሳዊ ምስክርነት ለኋለኛው ቀን ቅዱሳን መቀየር አስፈላጊ ነው። በተደጋጋሚ መታደስ ያለበት ነው። ይህም ካልሆነ፣ መንፈሳዊ ስሜቶች ይፈዛሉ እናም ይሰማት የነበረው(ራ) ሀይልን ለማስታወስ አይችልም ወይም አትችልም። ሰዎቹ እነዚያን ምልክቶች እናም የሰሟቸውን አስገራሚ ነገሮች መርሳት ጀመሩ፣ እናም ከሰማይ በሆነው አስገራሚ ምልክት መደነቃቸው መቀነስ ጀመረ፤ በዚህም ልባቸው መደንደን እናም አዕምሮአቸው መታወር ጀመረ፣ እናም ያዩአቸውን እናም የተመለከቱአቸውን በሙሉ አለማመን ጀመሩ…የክርስቶስን ትምህርት በተመለከተ የሞኝ እናም ከንቱ ነገር መሆኑን እንዲያምኑ መርቷቸዋል” (3 ኔፊ 2፥1–2)።

  22. ኤፌሶን 4፥11–14

  23. Thomas S. Monson, “Be of Good Cheer,” Liahona, May 2009, 92።

  24. ከሽማግሌ ፖርተር ኦፕንሾ የነበረ የግል ደብዳቤ፣ ነሀሴ 23፣ 2015።

  25. በቤተሰብ አባሉ መቃብር ላይ ፖርተር ኦፕንሿ የተናገራቸው፣ ሰኔ 22፣ 2015።