2010–2019 (እ.አ.አ)
ግድ የሚያሰኝ የእግዚአብሔር ምስክርነት፥ መፅሐፈ ሞርሞን
ጥቅምት 2017 (እ.አ.አ)


ግድ የሚያሰኝ የእግዚአብሔር ምስክርነት፥ መፅሐፈ ሞርሞን

መፅሐፈ ሞርሞን የኢየሱስ ክርስቶስ መለኮትነት፣ የጆሴፍ ስሚዝ የትንቢት ጥሪ፣ እናም የዚህች ቤተክርስቲያን ፍጹም እውነትነት ያለጥርጥር የሚያሳይ የእግዚአብሔር ምስክር ነው።

መፅሐፈ ሞርሞን የሃይማኖታችን የማዕዘን ድንጋይ ብቻ ሳይሆን፣ ነገር ግን ፈተናዎች ወይም ያልተመለሱ ጥያቄዎች ሲቀርቡብን፣ ምስክርነታችንን በአስተማማኝ ሁኔታ ሊይዝ የሚችል የምስክርነታችንም ጭምር የማዕዘን ድንጋይ ነው። ይህ መጽሐፍ የእውነት ሚዛን ላይ ሲመዘን የሁሉንም የተቃውሞ ክርክር የጋራ ክብደታቸውን ያሸንፋል። ለምን? ምክንያቱም እውነት ከሆነ፣ ጆሴፍ ስሚዝ ነቢይ ነበር እናም ምንም ዓይነት ታሪካዊ ወይም ሌላ ተቃራኒዎች ቢኖሩም፣ ይህ የተመለሰው የእየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስትያን ነው። ተቺዎች የመፅሐፈ ሞርሞንን ሀሰት እንደሆነ ለማስረዳት ያቀዱ ናቸው፣ ሆኖም ግን ይህ መጽሐፍ እውነት በመሆኑ ምክንያት ለሚያጋጥመው መሰናክል የማይሸነፍ ነው።

በመጀመሪያ፣ ተቺዎቹ፣ የ 23 ዓመት እድሜ ያለው ጆሴፍ ስሚዝ፣ ውስን ትምህርት ያለው የእርሻ ልጅ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ልዩ ስሞችና ቦታዎችን፣ እንዲሁም ዝርዝር ታሪኮች እና ክስተቶችን የያዘ መጽሐፍ እንደፈጠረ ማስረዳት አለባቸው። በዚህም መሠረት፣ ብዙ ተቺዎች በመፅሐፈ ሞርሞን ውስጥ ያለውን ታሪካዊ ይዘት ለመፍጠር በብዙ መጻሕፍት እና ሌሎች የአካባቢውን ግብዓቶች ላይ የተመሰረተና የፈጠራ ችሎታ ያለው ሰው ነው የሚል ሐሳብ ያቀርባሉ። ነገር ግን ከነሱ ድምዳሜ በተቃራኒ፣ ትርጓሜው ከመጀመሩ በፊት ጆሴፍን ከነዚህ ከተነገረላቸው ግብዓቶች ጋር እንዳየው የሚናገር ብቸኛ ምስክር የለም።

ምንም እንኳን ይህ ክርክር እውነት ቢሆን እንኳን፣ የመፅሐፈ ሞርሞን ህልውናን ለማብራራት በሚገርም ሁኔታ በቂ አይደለም። ጆሴፍ እነዚህን ሁሉ ያሏቸውን ግብዓቶች እንዴት አነበበ፣ የማይረባውን አንጥሮ፣ ማን እና የት እንዳለ እና መቼ የሚሉትን የረቀቁ እውነታዎችን በቀጥታ በመጠበቅ፣ ከዛም በፍጹም ትውስታው እንዴት ተረጎመው? ምክንያቱም ጆሴፍ ስሚዝ ሲተረጉም ምንም ማስታወሻ አልነበረውም። እንዲያውም ሚስቱ ኢማ እንዲህ በማለት ትዝታዋን ተናገረች፤ “እሱ ምንም ጥንታዊ ፅሁፍም ሆነ መጽሐፍ አልነበረውም። … እንደዚያ ዓይነት ነገር ቢኖረው ኖሮ ከእኔ ሊደብቀው ባልተቻለው ነበር።”1

ታዲያ እንዴት ነው ጆሴፍ ያለ ምንም ማስታወሻ 500-ገጽ በላይ መጽሐፍ በመጻፍ ይህን አስደናቂ ሥራ ያከናወነው? ይህንን ለማድረግ የፈጠራ ችሎታ ብቻ ሳይሆን ሊኖረወ የሚገባው፣ እጅግ ከፍተኛ መጠን ያለው የፎቶግራፍ ትውስታ ሊኖረው በተገባው ነበር። ነገር ግን ያም እውነት ከሆነ ተቺዎቹ ለዚህ አስደናቂ ችሎታ ትኩረታቸውን ያላደረጉት ለምንድን ነው?

ሆኖም ገና ሌላም አለ። እነዚህ ክርክሮች ለመጽሐፉ ታሪካዊ ይዘት ላይ የሚያጠነጥኑ ናቸው። ትክክለኛዎቹ ችግሮች አሁንም አሉ፤ ጆሴፍ መንፈስን የሚያንፀባርቅ መጽሐፍ ያዘጋጀው እንዴት ነበር፣ እናም እንደዚህ ያለ ጥልቅ አስተምህሮዎች፣ አብዛኛዎቹ የጊዜውን ክርስቲያናዊ እምነቶች የሚገልጽ ወይም የሚቃረኑ ትምህርቶችን ያገኘው ከየት ነው?

ለምሳሌ፣ የመፅሀፈ ሞርሞን ከአብዛኞቹ የክርስትና እምነቶች በተቃራኒ፣ የአዳም ውድቀት አዎንታዊ እርምጃዎች መሆኑን ያስተምራል። በመፅሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለተገለጹትን የጥምቀት ቃል ኪዳኖችን ገልጿል።

በተጨማሪም፣ ጆሴፍ በክርስቶስ የሀጢያት ክፍያ ምክንያት እኛን ማንጻት ብቻ ሳይሆን ፍፁማን ያደርገናል የሚለውን ታላቅ ማስተዋል ያገኘው ከየት ነው? በአልማ 32 ላይ የሚገኘውን አስደናቂውን የእምነት ስብከት ከየት አገኘ? ወይንም የንጉስ በንጀሚንን ስብከት በአዳኝ የሀጢያት ክፍያ፣ ምናልባትም በዚህ ርዕሰ-ጉዳይ ሁሉ ላይ በጣም አስደናቂ የሆነውን ስብከት ከየት አገኘ? ወይንም የወይራ ዛፍ ውስብስብ እና በትምህርት የተሞላውን ተምሳሌትን ከየት አገኘ? ይህን ተምሳሌት በማነብበት ጊዜ፣ ውስብስብነቱን ለመከተል ታሪኩን መዘርጋት አለብኝ። ጆሴፍ ስሚዝ እነዚህን ስብከቶች ያለምንም ማስታወሻ እንዲሁ ከትውስታው ተረከ ብሎ ማመን ያስፈልገናልን?

ከዚህ ድምዳሜ በተቃራኒ፣ የእግዚአብሄር የጣት አሻራዎች በመጽሐፈ ሞርሞን ሁሉ ውስጥ ይገኛሉ፣ አስደናቂ በሆኑት የትምህርት እውነቶች፣ በተለይም ደግሞ በኢየሱስ ክርስቶስ የኃጢያት ክፍያ ላይ የተሰጡት ታላቅ ትምህርቶች መረጃዎቹ ናቸው።

ጆሴፍ ነቢይ ካልሆነ፣ ለእነዚህ እና ለሌሎች በርካታ አስደናቂ ትምህርቶች ግንዛቤዎች ምላሽ ለመስጠት፣ ተቺዎች እሱ የሥነ-መለኮት ልሂቅ ነው ብለው መከራከር አለባቸው። ነገር ግን ይህ ከሆነ፣ አንዱ እንዲህ ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፣ የክርስቶስ አገልግሎትን ተከትሎ በ 1800ኛው ክፍለ ዘመን እንዲህ አይነት ሰፊ ልዩ እና ገላጭ ትምህርቶችን ለማምጣት ለምንድንነው ጆሴፍ ብቸኛ የሆነው? ምክንያቱም የዚህ መጽሐፍ ምንጭ ራዕይ እንጂ ሳይሆን የእውቀት ብሩህነት አይደለም።

እንዲህም ሆኖ ጆሴፍ በፈጠራና በስነ-መለኮት ተሰጦ የተካነ፣ የፎቶግራፍ ትውስታ ያለው ነው ብለን ብናስብ እንኳ፣ እነዚህ ተሰጥኦዎች ብቻ የበሰለ ፀሐፊ አያደርጉትም። የመፅሀፈ ሞርሞንን ሕልውና ለማብራራት፣ ተቺዎቹ በ 23 ዓመቱ ጆሴፍ በተፈጥሮው የጽሁፍ ተሰጥዖ ያለው ነው የሚል አረማመድ ሊኖራቸው ይገባል። ካልሆነ ግን፣ በርካታ ስሞችን፣ ቦታዎችን እና ክንዋኔዎችን ያለምንም ግራ ማጋባት እንዴት አድርጎ አቆራኛቸው? እንዴት አድርጎ የጦር ስልቶችን ዝርዝር አቀረበ፣ አንደበተ ርቱዕ ስብከቶችን ጻፈ እናም በሚሊዮኖች በሚቆጠሩ ህዝቦች ጎልተው የተቀመጡ ሃረጎችን ፈጠረ፣ በቃል የተያዙ፣ በማስታወሻነት በማቀዝቀዣ ላይ የተቀመጡ ለምሳሌ " እናንተ ሰዎችን በምታገለግሉበት ጊዜ እግዚአብሄርን እያገለገላችሁ እንደሆነ እርግጠኛ ትሆናላችሁ።”(ሞዛያ 2፥17) ወይም “ሰዎች እንዲኖሩ ደስታም ይኖራቸው ዘንድ” (2 ኔፊ 2፥25). እነዚህ የልብ ምት ያላቸው፣ የሚኖሩ እናም የሚተነፍሱ እና የሚያነሳሱ መልዕክቶች ናቸው። በ 23 ዓመት እድሜው ጆሴፍ ስሚዝ ይህን ታላቅ ስራ በአንድ ረቂቅ ጽሁፍ፣ በግምት በ65 የሥራ ቀናት ውስጥ ጻፈ ብሎ ማሰብ የህይወት እውነታዎችን መቃረን ማለት ነው።

ፕሬዚዳንት ራስል  ኤም ኔልሰን፣ ልምድ ያላቸውና የተካኑ ጸሐፊ፣ ከቅርብ ጊዜ ያቀረቡትን የጠቅላላ ጉባዔ ንግግር ከ 40 ጊዜአት በላይ ደጋግመው እንደጻፉት ተናግረዋል። አሁን ጆሴፍ ስሚዝ፣ በራሱ ብቻ፣ ጠቅላላ መፅሐፈ ሞርሞንን በአንድ ረቂቅ ጽሁፍ ጻፈው ማለት ነውን፣ ከጊዜአት በኋላ የተደረጉ ጥቂት ሰዋሰዋዊ ለውጦች በስተቀር?

የጆሴፍ ሚስት ኤማ እንዲህ ያለውን ተግባር የማይቻል መሆኑን ስታረጋግጥ እንዲህ አለች፤ “ጆሴፍ ስሚዝ [ወጣት እያለ] ግልጽ እና ጥሩ የቃላት ቅንብር ያለው ደብዳቤ መጻፍ አይችልም፤ እንደ መፅሐፈ ሞርሞን አይነት መጽሐፍ ምጻፍን ቀርቶ።”2

በመጨረሻም፣ አንድ ሰው ከላይ የተጠቀሱትን ክርክሮች ሁሉ ቢቀበለውም፣ አመጸኛ ቢመስልም፣ አሁንም ቢሆን ተቺዎች ሌላ የሚያደናቅፍ ችግር ይገጥማቸዋል። ጆሴፍ መፅሐፈ ሞርሞን በወርቅ ሰሌዳዎች ላይ እንደተጻፈ ተናገረ። ይህንንም በማለቱ በዘመኑ የማያቋርጥ ትችት ተሰነዘረበት፣ “ሁሉም” ሰዎች፣ ከብዙ ዓመታት በኋላ የጥንት ጽሑፎች በብረት ሰሌዳዎች ላይ እስኪገኙ ድረስ፣ ጥንታዊ ታሪኮች በፓፒረስ ወይም በብራና ላይ እንደሚጻፉ ያውቁ ነበር፣ በተጨማሪም ተቺዎች፣ የጥንታዊ አሜሪካ አገሮች የሲሚንቶ መዋቅሮች እስከሚገኙበት ድረስ፣ በመፅሐፈ ሞርሞን ውስጥ እንደተገለጸው ሲሚንቶ መጠቀም በእነዚህ ጥንታዊ አሜሪካውያን የቴክኒካዊ እውቀት በላይ ነው ይሉ ነበር። በአሁኑ ጊዜስ ተቺዎች የእነዚህን እና ተመሳሳይ ግኝቶችን እንዴት ያቀርቡታል? ጆሴፍ፣ ተመልከቱ እንግዲህ፣ እጅግ በጣም ጥሩ ዕድለኛ ገማች መሆን አለበት። ምንም እንኳን ሁሉም በሱ ላይ ተቃራኒ ቢሆኑም፣ አሁንም ባሉ ሳይንሳዊ እና የትምህርት እውቀቶች በተቃራኒ፣ ሌሎች ስህተት በሆኑበት ሰአት እሱ በትክክል ገምት።

ሁሉም ከተነገሩ እና ከተፈጸሙ በኋላ፣ አንድ ሰው በእነዚህ ተቺዎች እንደተነገረው የተባለላቸው ሁኔታዎች እና ሀይሎች በድንገት በመደራረብ ጆሴፍን መፅሐፈ ሞርሞንን እንዲጽፍ እና ሰይጣናዊ ፈጠራን ሊያስፋፋ ቻለ ብለው ይገረማሉ። ግን ይህ እንዴት ትርጉም ይሰጣል? ይህንን አመለካከት በቀጥታ በሚቃረን መልኩ፣ ይህ መጽሐፍ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ሰይጣንን እንዲቃወሙ እና ክርስቶስን የሚመስል ህይወትን እንዲኖሩ አነሳስቷቸዋል።

አንድ ሰው የተቺዎቹን የማገናዘቢያ መንገድ ለማመን ቢመርጥም፣ ለእኔ ግን፣ ለአዕምሮ እና ለመንፈስ የተቋጨ ጉዳይ ነው። እንደዚህ ያሉትን ለማመን፣ ያልተረጋገጠ ሃሳቦችን አንዱን ከሌላው አከታትዬ መቀበል አለብኝ ማለት ነው። በተጨማሪም፣ 11 ምስክሮች ምስክርነትን3 ችላ ማለት አለብኝ፣ ምንም እንኳን እስከ መጨረሻው ድረስ ለምስክርነታቸው ታማኝ ሆነው ቢቀጥሉም፤ በመለኮታዊ ትምህርቶች ከገጽ ገጽ የተሞላውን ይህን የተቀደሰ መጽሃፍ አልቀበልም ማለት አለብኝ፤ ይህንን መጽሐፍ በማንበብ እራሴን ጨምሮ፣ ብዙ ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር ከማንኛውም መጽሃፍ በላይ ቅርብ የማድረጉን ሃቅ ችላ ማለት አለብኝ። የመንፈስ ቅዱስን የማረጋገጫ ሹክሹክታ መሻር አለብኝ። ይህ እውነት እንደሆነ ከማውቀውን ሁሉ ተቃራኒ ነው።

አንዱ ጥሩ እና ብሩህ ጓደኞዬ ከቤተ ክርስቲያን ለጊዜው ለቆ ነበር። በቅርብ ጊዜ ስለመመለሱ ሲጽፍልኝ እንዲህ አለ፤ በመጀመሪያ፣ መፅሐፈ ሞርሞን በታሪክ፣ በጂኦግራፊ፣ በቋንቋ እና በባህል እንዲያረጋገጥልኝ ፈልጌ ነበር። ነገር ግን ስለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል እና ስለደህንነት ተልዕኮው በሚያስተምረው ላይ ለማተኮር ስቀይር፣ ስለእውነንተቱ ምስክርነቴን ማግኘት ጀመርኩኝ። አንድ ቀን በክፍሌ ውስጥ መፅሐፈ ሞርሞንን እያነበብኩኝ እያለሁ፣ ማንበብ አቆምኩኝ፣ ተንበረከኩኝ፣ እናም በልብ የተሰማ ጸሎት ሰጠሁ እናም የሰማይ አባት ለመንፈሴ ቤተክርስቲያኗ እና መፅሐፈ ሞርሞን እውነት እንደሆኑ በማረጋገጥ ሲያንሾካሽክልኝ ተሰማኝ። የሶስት ዓመት ከግማሽ የወሰደብኝ የቤተ ክርስቲያኗን ዳግም የመመርመር ጊዜ እውነታውን በሙሉ ልብ እና በሙሉ አሳማኝ በሆነ መንገድ እንድመልስ አደረገኝ።

አንድ ሰው ልክ እንደ ጓደኛዬ መፅሐፈ ሞርሞንን ለማንበብ እና ለማሰላሰል ጊዜ የሚወስድ ከሆነ እና የመንፈስ ቅዱስ ጣፋጭ ፍራፍሬዎችን በትኩረት ከተከታተለ ከዚያ በኋላ እሱ / እሷ የፈለገውን ምስክርነት ይቀበላሉ።

መፅሐፈ ሞርሞን በዋጋ ሊተመን የማይችል የእግዚአብሔር ስጦታዎች አንዱ ነው። እርሱም ሰይፍና ጋሻ ነው - የእግዚአብሔርን ቃል ለጻድቃን ልቦች ለመዋጋት ወደ ጦርነቱ ይልካልና የእውነት ዋና መከላከያ ሆኖ ያገለግላል። እንደ ቅዱሳን፣ ለመፅሐፈ ሞርሞን ለመከላከል ብቻ ሳይሆን ግዴታ እና እድል ያለን፣ ለማጥቂያነት ለመጠቀም፣ መለኮታዊ ትምህርቶቹን በሀይል ለመስበክ እና ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር ስላለው አስደናቂ ምስክርነት ለመጋበዝ እድል አለን።

መፅሐፈ ሞርሞን በእግዚአብሔር ስጦታና ኃይል እንደተተረጎመ የእኔን ክቡር ምስክርነት እሰጣለሁ። የኢየሱስ ክርስቶስ መለኮት፣ የጆሴፍ ስሚዝ የትንቢት ጥሪ፣ እናም የዚህች ቤተ ክርስቲያን ፍጹም እውነትነት የእግዚአብሔር ግድ የሚያሰኝ ምስክር ነው። ይህ የእኛ ምስክርነት የማእዘን ድንጋይ ይሁን፣ ስለዚህም ልክ እንደ ተለወጡት ላማውያን እንደተባለው ሁሉ ስለ እኛም "ፈጽሞ አልወድቁም” ይባል ዘንድ (አልማ 23፥6)። በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።

ማስታወሻዎች

  1. Emma Smith, in “Last Testimony of Sister Emma,” Saints’ Herald, Oct. 1, 1879, 289, 290.

  2. Emma Smith, in “Last Testimony of Sister Emma,” 290.

  3. “የሶስት ምስክሮች ምስክርነት” እና “የስምንት ምስክሮች ምስክርነት” መፅሐፈ ሞርሞን ተመልከቱ።