ቅዱሳት መጻህፍት
፪ ኔፊ ፲፬


ምዕራፍ ፲፬

ፅዮንና ሴቶች ልጆችዋ ይድናሉ፣ እናም በሺኛው ዘመን ይነፃሉ—ኢሳይያስ ፬ን አነጻፅሩ። ከ፭፻፶፱–፭፻፵፭ ም.ዓ. ገደማ።

እናም በዚያ ቀን፣ ሰባት ሴቶች አንድን ወንድ ይይዛሉ፣ የራሳችንን ዳቦ እንበላለን፣ እንዲሁም የራሳችንን ልብስ እንለብሳለን፣ ሀፍረታችንን ለማስወገድ በስምህ ብቻ እንጠራ ይላሉ።

በዚያ ቀን የጌታ ቅርንጫፍ ያማረና የከበረ ይሆናል፤ ከእስራኤል ለመጡት የምድሪቱ ፍሬ ታላቅና ውብ ይሆናል።

እናም እንዲህ ይሆናል፣ በፅዮን የቀሩና በኢየሩሳሌም የቀሩ፣ በኢየሩሳሌም በሕያዋን መካከል የተመዘገቡ ሁሉ ቅዱስ ተብለው ይጠራሉ—

ጌታ የፅዮንን ሴት ልጆች እድፍ ባጠበ ጊዜ፣ እና የኢየሩሳሌምንም ደም በፍርድ መንፈስና በሚያቃጥል መንፈስ ከመካከልዋ ባነፃ ጊዜ ቅዱስ ተብለው ይጠራሉ።

እናም ጌታ በፅዮን ተራራ ባለ ማደሪያ ላይና፣ በመሰብሰቢያዎቿ ላይ፣ በቀን ደመናንና፣ ጢስን በሌሊትም የሚበራውን የእሳት ብርሃን ይፈጥራል፤ በፅዮን ክብር ሁሉ ላይ መጋረጃ ይሆናልና።

እናም በቀን ከሙቀት ለመጠለያ ቦታ፣ ለመሸሸጊያም ቦታ፣ እናም ከውሽንፍርና ከዝናብ መሸፈኛ ድንኳን ይሆናል።