መመሪያ መጻህፍቶች እና ጥሪዎች
2. በደህንነት እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ስራ ውስጥ ግለሰቦችን እና ቤተሰቦችን መደገፍ


“2. በደህንነት እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራ ውስጥ ግለሰቦችን እና ቤተሰቦችን መደገፍ፣” ከአጠቃላይ የመመሪያ መፅሐፍ የተመረጡ [2023(እ.አ.አ)]።

“2. በደህንነት እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራ ውስጥ ግለሰቦችን እና ቤተሰቦችን መደገፍ፣” ከአጠቃላይ የመመሪያ መፅሐፍ የተመረጡ

ምስል
የቤተሰብ ፎቶ

2.

በደህንነት እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራ ውስጥ ግለሰቦችን እና ቤተሰቦችን መደገፍ

2.0

መግቢያ

በኢየሱስ ከርስቶስ ቤተክርስቲያን ውስጥ መሪ እንደመሆናችሁ፣ ግለሰቦች እና ቤተሰቦች የደህንነትን እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግን ሥራ እንዲያከናውኑ ትረዳላችሁ (1.2 ይመልከቱ)። የዚህ ስራ የመጨረሻ አላማ የእግዚአብሔር ልጆች ሁሉ የዘለአለም ህይወትን በረከቶች እና የደስታ ሙላት እንዲያገኙ መርዳት ነው።

ብዙው የደህንነት እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራ የሚከናወነው በቤተሰብ አማካኝነት ነው። ለሁሉም የቤተክርስቲያኗ አባላት፣ ይህ ስራ ቤትን ያማከለ ነው።

2.1

በእግዚአብሔር እቅድ ውስጥ ቤተሰብ ያለው ሚና

እንደ እቅዱ ክፍል የሰማይ አባት ቤተሰብን በምድር አቋቁሟል። ቤተሰቦች ደስታን እንዲያመጡልን ይፈልጋል። ቤተሰቦች የመማር፣ የማደግ፣ የማገልገል፣ ንስሃ የመግባት እና ይቅር የማለት እድሎችን ይፈጥራሉ። የዘለአለም ህይወትን ለማግኘት እንድንዘጋጅ ሊረዱን ይችላሉ።

እግዚአብሔር የሰጠው የዘለአለም ህይወት ተስፋ ዘለአለማዊ ጋብቻን፣ ልጆችን እና ሁሉንም የዘለአለም ቤተሰብ በረከቶችን ያካትታል። ይህ የተስፋ ቃል በአሁኑ ጊዜ ያላገቡትን ወይም በቤተክርስቲያኗ ውስጥ ቤተሰብ የሌላቸውንም ይመለከታል።

2.1.1

ዘለአለማዊ ቤተሰቦች

የቤተክርስቲያኗ አባላት በቤተመቅደስ ውስጥ የመታተም ሥርዓቶችን በሚያከናውኑበት ጊዜ ቃል ኪዳን ሲገቡ፣ ዘለአለማዊ ቤተሰቦችን ይመሰረታሉ። አባላት እነዚያን ቃል ኪዳኖች ሲጠብቁና መጠበቅ ባልቻሉ ጊዜም ንስሃ ሲገቡ የዘለአለም ቤተሰብ በረከቶች እውን ይሆናሉ። አባላት እነዚህን ሥርዓቶች ለመቀበል እንዲዘጋጁ እና ቃል ኪዳኖቻቸውን እንዲያከብሩ የቤተክርስቲያን መሪዎች ይረዷቸዋል።

ዘለአለማዊ ቤተሰቦችን የማቋቋም ተጨማሪ ገፅታው አባላት በቤተመቅደስ ከሞቱ ቅድመ ዓያቶቻቸው ጋር ለመታተም የሚያስችሏቸውን ሥርዓቶች ማከናወን ነው።

2.1.2

ባል እና ሚስት

በወንድ እና በሴት መካከል የሚደረግ ጋብቻ በእግዚአብሔር የተመሰረተ ነው (ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 49፥15 ይመልከቱ)። አንድ ባልና ሚስት በአንድነት ወደ ዘለአለማዊ ህይወት እድገት እንዲያደርጉ የታሰቡ ናቸው (1 ቆሮንቶስ 11፥11)።

የዘለአለም ህይወትን ለማግኘት ከሚያስፈልጉ መስፈርቶች አንዱ፣ ወንድና ሴት የሰለስቲያል ጋብቻ ቃል ኪዳን መግባት ነው (ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 131፥1–4 ይመልከቱ)። ጥንዶች በቤተመቅደስ ውስጥ የጋብቻ እትመት ሥርዓትን ሲያከናውኑ ይህን ቃል ኪዳን ይገባሉ። ይህ ቃል ኪዳን የዘለአለማዊ ቤተሰብ መሰረት ነው። በታማኝነት ከተጠበቀ፣ ትዳራቸው ለዘለአለም ጸንቶ እንዲኖር ያስችላል።

በባልና በሚስት መካከል ያለው አካላዊ መቀራረብ ያማረ እና የተቀደሰ እንዲሆን የታሰበ ነው። ልጆችን ለመፍጠር እንዲሁም በባልና በሚስት መካከል ያለን ፍቅር ለመግለፅ በእግዚአብሔር የተመሰረተ ነው። የቅርብ ግንኙነታቸውን መምራት ያለበት ርኅራኄ እና አክብሮት እንጂ ራስ ወዳድነት መሆን የለበትም።

እግዚአብሔር የሚደረገው ያ ጾታዊ መቀራረብ በአንድ ሴት እና በአንድ ወንድ መካከል መሆን እንደሚገባው አዝዟል።

ባል እና ሚስት በእግዚአብሔር ፊት እኩል ናቸው። አንዱ ሌላውን መጨቆን የለበትም። ውሳኔዎቻቸው የሚደረጉትም በሁለቱም ሙሉ ተሳትፎ፣ በአንድነት እና በፍቅር መሆን አለበት።

2.1.3

ወላጆች እና ልጆች

የኋለኛው ቀን ነቢያት፣ ”እንዲባዙ እና ምድርን ይሞሉ ዘንድ እግዚአብሔር ለልጆቹ የሰጠው ትእዛዝ አሁንም በተግባር የሚውል ነው” ሲሉ አስተምረዋል (“ቤተሰብ፦ ለአለም የተላለፈ አዋጅ፣” በተጨማሪም ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 49፥16–17ን) ይመልከቱ።

አፍቃሪ የሆኑ ባልና ሚስት ልጆችን በጋራ ለማሳደግ እና ለመንከባከብ ከሁሉ የተሻለውን ቦታ ይፈጥራሉ። ግለሰባዊ ሁኔታዎቻቸው ወላጆች ልጆቻቸውን በጋራ እንዳያሳድጉ ሊያደርጓቸው ይችላሉ። ሆኖም፣ የእርሱን እርዳታ ሲሹ እና ከእርሱ ጋር የገቡትን ቃል ኪዳን ለመጠበቅ ጥረት ሲያደርጉ ጌታ ይባርካቸዋል።

ወላጆች ልጆቻቸው የዘለዓለም ህይወት በረከትን ለማግኘት እንዲዘጋጁ የመርዳት እጅግ አስፈላጊ ኃላፊነት አለባቸው። ልጆቻቸው እግዚአብሔርን እና ሌሎችን እንዲወዱ እና እንዲያገለግሉ ያስተምራሉ (ማቴዎስ 22፥36–40ን ይመልከቱ)።

“አባቶች በፍቅር እና በጻድቅነት ቤተሰቦቻቸውን ያስተዳድራሉ እና ለቤተሰቦቻቸው የህይወት መሰረታዊ ፍላጎት የማሟላት እና ጥበቃ ኃላፊነት አለባቸው (“ቤተሰብ፦ ለዓለም የተላለፈ ዓዋጅ”)። በቤት ውስጥ ባል ወይም አባት ከሌለ እናትየው ቤተሰቡን በበላይነት ትመራለች።

ቤተሰብን በበላይነት መምራት ማለት የቤተሰብ አባላት ተመልሰው ከእግዚአብሔር ጋር እንዲኖሩ የመምራት ኃላፊነት ነው። ይህም የሚሆነው የኢየሱስ ክርስቶስን ምሳሌ በመከተል በየዋህነት፣ በደግነት እና በንጹህ ፍቅር በማገልገል እና በማስተማር ነው (ማቴዎስ 20፥26–28 ይመልከቱ)። ቤተሰብን በበላይነት መምራት የቤተሰብ አባላትን በዘወትር ጸሎት፣ በወንጌል ጥናት እና በሌሎች የአምልኮ ዘርፎች መምራትን ያካትታል። ወላጆች እነዚህን ኃላፊነቶች ለመወጣት በህብረት ይሰራሉ።

“እናቶች በቀደምትነት ልጆቻቸውን የመንከባከብ ኃላፊነት አለባቸው” (“ቤተሰብ፦ ለዓለም የተላለፈ ዓዋጅ”)። መንከባከብ ማለት የአዳኙን ምሳሌ በመከተል መመገብ፣ ማስተማር እና መደገፍ ማለት ነው (3 ኔፊ 10፥4ን ይመልከቱ)። እናት ከባለቤቷ ጋር በመተባበር ቤተሰቧ የወንጌልን እውነቶች እንዲማሩ እንዲሁም በሰማይ አባት እና በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያላቸውን እምነት እንዲያሳድጉ ትረዳቸዋለች። በአንድነት በቤተሰብ ውስጥ የፍቅር አካባቢን ይፈጥራሉ።

”በእነዚህ ቅዱስ ኃላፊነቶችም፣ አባቶች እና እናቶች በእኩል አጋርነታቸው የመረዳዳት ኃላፊነት አለባቸው” (“ቤተሰብ፦ ለዓለም የተላለፈ ዓዋጅ”)። በጸሎት መንፈስ በጋራ እንዲሁም ከጌታ ጋር ይመካከራሉ፡፡ ውሳኔዎቻቸው የሚደረጉትም በሁለቱም ሙሉ ተሳትፎ፣ በአንድነት እና በፍቅር መሆን አለበት።

2.2

የደህንነት እና በዘአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራ በቤት

ቀዳሚ አመራር እንዲህ ብለዋል፣ “ቤት የፅድቅ ህይወት መሰረት ነው” [የቀዳሚ አመራር ደብዳቤ፣ የካቲት 11፣ 1992 (እ.አ.አ)]።

አባላት በቤት የደህንነት እና በዘለዓማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራን እንዲሰሩ ለመርዳት የቤተክርስቲያን መሪዎች መንፈሱ ያለበትን ቤት እንዲፈጥሩ ያበረታቷቸዋል። በተጨማሪም አባላት የሰንበትን ቀን እንዲያከብሩ፣ በቤት ውስጥ ወንጌልን እንዲያጠኑ እና እንዲማሩ እንዲሁም ሳምንታዊ የቤት ምሽት እንዲያካሂዱ ያበረታታሉ።

2.2.3

የወንጌል ጥናት እና ትምህርት በቤት

የወንጌል መማር ማስተማር በቤትን ያማከሉ እና በቤተክርስቲያን የተደገፉ ናቸው። የቤተክርስቲያን መሪዎች ሁሉም አባላት በሰንበት ቀን እንዲሁም በሳምንቱ በሁሉም ቀናት በቤት ውስጥ ወንጌልን እንዲያጠኑ ያበረታታሉ።

ኑ፤ ተከተሉኝ—ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች ውስጥ በተዘረዘረው መሰረት፣ ቅዱሳት መጻህፍትን ማጥናት የሚመከር በቤት ውስጥ ወንጌልን የማጥናት መንገድ ነው።

2.2.4

የቤተሰብ ምሽት እና ሌሎች አክቲቪቲዎች

የኋለኛው ቀን ነቢያት፣ የቤተከርስቲያን አባላት ሳምንታዊ የቤት ምሽት እንዲያካሂዱ መክረዋል። ይህ ግለሰቦች እና ቤተሰቦች ወንጌልን የሚማሩበት፣ ምስክርነቶችን የሚያጠናክሩበት፣ አንድነትን የሚገነቡበት እና አንዳቸው ሌላውን የሚያስደሰቱበት የተቀደሰ ቀን ነው።

የቤት ምሽት እንደአባላቶች ሁኔታ የሚለዋወጥ ሊሆን ይችላል። በሰንበት ቀን ወይም በሌላ ቀን እና ሰዓት ሊካሄድ ይችላል። የሚከተሉትን ሊያካትት ይችላል፦

  • የወንጌል ጥናት እና መመሪያ (የኑ፤ ተከተሉኝ መርጃዎች እንደተፈለገ ጥቅም ላይ ሊውሉ ይችላሉ)።

  • ሌሎችን ማገልገል።

  • መዝሙሮችን እና የመጀመሪያ ክፍል መዝሙሮችን መዘመር እና ማጫወት (ምዕራፍ 19ን ይመልከቱ)።

  • የቤተሰብ አባላትን በልጆች እና ወጣቶች እድገት መደገፍ።

  • ግብ ለማውጣት ችግሮችን ለመፍታት እና መርሃ ግብሮችን ለማስተባበር የቤተሰብ ምክር ቤት ማካሄድ።

  • የመዝናኛ ተግባራት

ያላገቡ አባላት እና ሌሎች፣ በቤት ምሽት ለመሳተፍ እና በወንጌል ጥናት አንዳቸው ሌላውን ለማጠናከር ከመደበኛው የሰንበት አምልኮ ፕሮግራም ውጪ በሌሎች ቡድኖች ሊሰባሰቡ ይችላሉ።

2.2.5

ግለሰቦችን መደገፍ

የቤተክርስቲያን መሪዎች የሚደግፍ ቤተሰብ የሌላቸውን አባላት ይረዳሉ።

መሪዎች፣ እነዚህ አባላት እና ቤተሰቦቻቸ የወዳጅነት ኅብረት፣ ጤናማ ማህበራዊ ልምዶች እና የመንፈሳዊ እድገት እድሎች እንዲኖሯቸው ይረዷቸዋል።

2.3

በቤተክርስቲያን እና በቤት መካከል ያለ ግንኙነት

የደህንነት እና በዘለአለማዊ ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ሥራ ቤትን ማዕከል ያደረገ እና በቤተክርስቲያን የተደገፈ ነው። በቤተክርስቲያኗ እና በቤት መካከል ያለ ግንኙነትን በተመለከተ የሚከተሉት መርሆዎች ተግባራዊ ይደረጋሉ።

  • መሪዎች እና አስተማሪዎች የወላጆችን ሚና ያከብራሉ እንዲሁም ይረዷቸዋል።

  • አንዳንድ የቤተክርስቲያን ስብሰባዎች በእያንዳንዱ አጥቢያ እና ቅርንጫፍ ውስጥ በጣም አስፈላጊ ናቸው። እነዚህም የቅዱስ ቁርባን ስብሰባን እና የትምህርት ክፍል እንዲሁም የቡድን ስብሰባዎችን ያካትታሉ። ብዙዎቹ ሌሎች ስብሰባዎች፣ አክቲቪቲዎች እና ፕሮግራሞች የግድ አስፈላጊ አይደሉም።

  • የቤተክርስቲያን አገልግሎት እና ተሳትፎ መስዋዕትነትን ይጠይቃል። አባላት በእርሱ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሲያገለግሉ እና መስዋዕትነት ሲከፍሉ ጌታ ይባርካቸዋል። ሆኖም፣ ለቤተክርስቲያን አገልግሎት የሚሰጠው ጊዜ አባላት በቤት፣ በሥራ ቦታ እና በሌሎች ቦታዎች ያሉባቸውን ኃላፊነቶች ለማክበር እንዳይችሉ ማድረግ የለበትም።